|
“እኔን የወደደ መስቀሌን ይዞ ይከተለኝ” |
መንግሥትበልማት ስም ቅዱስና ታሪካዊ የሆነውን የዋልድባን ገዳም ተጠግቶ የስኳር ፋብሪካ እገነባለሁ ካለ ጊዜ ጀምሮ ጉዳዩ ከአገር አልፎ በዓለም ዙሪያ ያሉ ኢትዮጵያዊያንን በስፋት ሲያነጋግር ሰንብቷል። ዋልድባ ለክፍለ ዘመናት ታፍሮና ተከብሮ “በጥብቅ” ሀይማኖታዊ ስርዓት የቆየ፣ ፍጹም ልዩ የሆነ መንፈሳዊና ታሪካዊ ዋጋ ያለው ስፍራ እንደመሆኑ በስፋት እየቀረበ ያለው ተቃውሞም በከፍተኛ ስሜት እና ቁጣ የታጀበ ሊሆን ችሏል።
እኔም ችግሩ የአንድ ወቅት ትኩሳት ሆኖ የማይቆም፤ ይልቅስ የማንነት፣ የታሪክና የዕምነት ፅናት ጥያቄ መሆኑን በማመኔ ነበር በስፍራው ተገኝቼ ሁኔታውን መመርመር እንዳለብኝ የወሰንኩት። ያዩ፣ የሰሙትንና የታዘቡትን ለህዝብ ማካፈሉ ደግሞ የሙያ ብቻ ሳይሆን የዜግነትም ግዴታ ይመስለኛል።
ዋልድባ ደርሼ የሆነውን ሁሉ ለመመርመር ያደረኩት ጥረት ግን በመስዋዕትነት የተከበበ፣ ብዙ ዋጋም ሊያስከፍለኝ ይችል እንደነበር መሸሸግ አልችልም። ከአ.አ. ጎንደር፣ ከጎንደር ዋልድባ ለመድረስ ያለው የጉዞ ርዝማኔ እንዳለ ሆኖ ከገዳሙ ለመድረስ ከ30 በላይ ኪሎ ሜትሮች ሲቀሩን ጀምሮ ያለው ጥብቅ ጥያቄና ምዝገባ ሁሉ እጅግ አስደንጋጭና ያልተለመደ ነው።
የተሳፈርኩበት አውቶብስ ዋልድባ ሊደርስ 35 ኪሎ ሜትር ያህል ሲቀረው ወደ ቀኝ ወደወልቃይት ፣ ቀጥታውን ደግሞ ወደ ዋልድባ የሚዘለቅበት መንገድ መገናኛ ስፍራ ላይ ትልቅ ኬላ ተሰርቷል። ይህ ስፍራ በአካባቢው ስዎች “ጉምድኝ” ተበሎ የሚጠራ ሲሆን ረቡዕ እና ቅዳሜ የደራ የገበያ ስፍራ እንደሚሆንም ተነግሮኛል። እዚህ ስፍራ ሲደረስ የዋልድባ ተጓዥ ወርዶ በሌላ መኪና መሳፈሩ የተለመደ ነውና እኔም ከዋልድባ መንገደኞች ጋር መውረድ ነበረብኝ። ነገር ግን ቀደም ብሎ በደረሰኝ መረጃ መሠረት እዚያ ስፍራ ላይ ያሉት የመንግሥትታጣቂዎች ወደ ዋልድባ የሚሄዱ ሠዎችን ስም በማጣራት ‘ወዴትና ለምን?’ እንደሚሄዱ በመጠየቅ የሚመዘግቡ በመሆናቸው የእኔ እዚያ ቦታ ተገኝቶ መመዝገብ አደገኛነቱ የታሰበኝ ከመኪና ሳልወርድ ነበር።
በመንግሥት አንጋቾች እጅ መውደቅ ምን ሊያስከትል እንደሚችል እያሰላሰልኩ የጉዞዬን ዓላማም ጭራሽ የማላሳካበት ዕድል እንዳይፈጠር ተገቢ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለብኝ ወሰንኩ። . . . በዚህም ወደቀኝ ታጥፈው ከሚዘልቁት የወልቃይት መንገደኞች ጋር ከመሄድ ውጭ አማራጭ
አልነበረኝም። በጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ውስጥ በወደቀው የአካባቢው ሁኔታ እየተገረምኩ ሁሉን በፍርሃትና በጥርጣሬ አይን እየቃኘሁ ለግማሽ ቀን በወልቃይት ዙሪያ “መክፈልት” በምትባለው የገጠር ቀበሌ ሆኜ ዋልድባን ከሩቅ በሃሳብ እየዋኘሁበት ተከታዩን ዘገባ አጠናቀርኩ።
በወልቃይትና በዋልድባ መካከል በሚፈሰው ዘረማ (ዛሬማ) ወንዝ መንግሥትለስኳር ልማት እየገነባ ያለው የመስኖ ፕሮጀክት ይሄን ያህል እንዴት ትኩረት ሊሰጠውና እንዲህ ሊያጨቃጭቅ ቻለ? የሚል ጥያቄ ማንሳት ተገቢና ወቅታዊም ይመስለኛል። ዋልድባ ሲባል እንደ ደብረ ሊባኖስ፣ ዝቋላ አቦ፣ ግሸን ማሪያም….ወዘተ በአንድ የተወሰነ ጠባብ ቦታና አጥር የተከለለ የሚመሰላቸው ሠዎች ጥቂት አይደሉም።
ዋልድባ ገዳምን ከበው ከያዙት (ከሚያዋስኑት) ወንዞች መካከል በምእራብ አቅጣጫ የሚገኘው ዘረማ ወንዝ አሁን ለስኳር ልማት ተብሎ የመስኖ ፕሮጀክት የተጀመረበት ነው። ይህንኑ ፕሮጀክት በሚመለከት ያነጋገረኩት አንድ የጎንደር ከተማ ነዋሪ ቅዱሳን አባቶች የሚጠልቁት ወንዝ በመሆኑ መንግስት ለስኳር ልማት መስኖ ፕሮጀክት መጠቀሙ መንፈሳዊነቱን ይጻረረዋል ብሎኛል። በገዳሙ ዙሪያ ከሚኖሩ መነኮሳት መካከል አንዱ የሆኑ አባት ግን «ቅዱሳት አባቶች ከማየ ዮርዳኖስ እንጂ ከዘረማ አይጠልቁም» ብለውኛል።
በገዳሙ አዋሳኝ ከሚገኘው ዘረማ ወንዝ ተጠልፎ እየተስራ ያልውን የመስኖ ልማት ፕሮጀክት በሚመለከት ያነጋገርኳቸው ሌላ አባት ደግሞ የስኳር ልማት ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ ከገዳሙ ውጪ የሚገኝ ቢሆንም ዘረማ ወንዝ በቅዱሳን መነኮሳት ዘንድ ከገነት የሚፈስ ተደርጎ የሚወሰድ በመሆኑ ‘ባይነካ ነበር ደግ’ ብለውኛል።
በወልቃይት እና በዋልድባ ገዳም አማካኝ ስፍራ ላይ የሚፈሰው የዘረማ ወንዝ ለአካባቢው ነዋሪ አርሶ አደሮች ከብቶቻቸውን ውሃ የሚያጠጡበት፣ ራሳቸውም እየጠለቁ ለቤት ውስጥ ፍጆታ የሚጠቀሙበት እንደሆነ የገለጹልኝ አንድ የአካባቢው ነዋሪ በበኩላቸው የሰኳር ልማት ፕሪጀክቱ ከገዳሙ ውጪ ያለ ቢሆንም ከስኳር ልማቱ ጋር በተያያዘ የሚመሰረተው መንደር የአካባቢውን ሠላማዊነት ሊረብሸው እንደሚችል ገልጸው ለፕሮጀክቱ ስራ ተብሎ በሚመሠረተው መንደር የሚሠፍሩት
ሠዎች የመሃል አገር ሰዎች መሆናቸውና የአካባቢውን ጥብቅ መንፈሳዊ ህግጋት የማያውቁ መሆናቸው መጪውን ጊዜ እንድንናፍቀው አያደርገንም ብለዋል።
በዋልድባ ገዳምና የስኳር ልማት ፕሮጀክቱ በሚሰራበት ስፍራ መካከል ርቀት መኖሩን የተረዱ ሠዎች ቁጥር በርካታ ቢሆንም ግንዛቢያቸው ከስጋት ነፃ አይደለም። ከፕሮጀክቱ ጋር ተያይዞ የሚፈጠረው መንደር ከመንደሩም ጋር ተያይዞ የሚመጡ ሰዋዊ ባህሪያት የሚፈጥሩት ያልተገባ ድርጊት በርቀትም ቢሆን የገዳሙን መለኮታዊ መልክ ሊረብሸው ይችላል የሚል ስጋት አለ። እዚህ ጋቀደም ብለን ያነሳነው አንድ ጥያቄ ተመልሶ ሊነሳ ይችላል።’ የዋልድባ ጉዳይ ይሄን ያህል እንዴት ትኩረት ሊሰጠውና ሊያጨቃጭቅ ቻለ?’ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ለመሻት አጠቃላዩን የገዳሙን ሁኔታ መቃኘቱ ተገቢ ይመስለኛል።
መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ
ዋልድባ በአራት ወንዞች የተከበበ/የታጠረ ቢባል ይሻላል/ አራት ማእዘን አይነት ቅርጽ ያለው የአንድ ወረዳ/አውራጃ/ ግዛት ያህል ስፋት ያለው አካባቢ ነው። በሌላ አገላለጽ ከደቡብ እስከ ሰሜን/ ከአርማሕ ደጋ እስከ ተከዜ/ ያለው ርቀት በግምት ከ120-150 ኪሎ ሜትር ሲሆን ከምስራቅ እስከ ምዕራብ ማለትም ከእንስየ ወንዝ እስከ ዘረማ ወንዝ ያለው ርቀት ደግሞ ከ60-70 ኪሎ ሜትር ይሆናል።
እንደዛም ሆኖ የዋልድባ ገዳም በደቡብ ሰፋ ያለ ሆኖ ወደ ተከዜ ወንዝ እየተጠጋ በመጣ ቁጥር እየጠበበ ሄዶ እስከ 30 ኪ.ሜ ይሆናል። አራቱ የዋልድባ አዋሳኝ ወንዞች በምስራቅ እንስየ፣ በምዕራብ ዘረማ፣ በሰሜን ተከዜ፣ በደቡብ ወይባ ናቸው። ከእነዚህ መካከል ትንሹ ወይባ ሲሆን በዋልድባ ደቡብ ካሉ ተራሮች ተነስቶ ጨው በርንና ዋልድባን እየለየ የተወሰነ ርቀት ከተጓዘ በኋላ ወደ እንስያ ይቀላቀላል።
“እህል አይቀመስበት፣ ሓጢያት አይሻገርበት” የተባለለት ዋልድባ በውስጡ ወይና ደጋና ቆላማ የአየር ንብረቶች ያካተተ በመሆኑ በቦታው የሚበቅሉ ዕጽዋት አይነት ቁጥር እጅግ በርካታ ናቸው። ለአብነት ያህል ደቅማ፣ ማቅማ፣ ጣበሌ፣ ወይባ፣ ዲማ/ፍርጣጣ/፣ ሸመል፣ እንኮይ፣ግራር/ሦስት አይነት/፣ወይላሆ፣ በትረ ያሬድ፣ አምፋር፣ አጋም፣ ኮርች፣ ወዘተ በዋልድባ በብዛት የሚበቅሉ ናቸው። ከትላልቅ ዛፎች በተጨማሪ ቁጥራቸው የበዛ የሐረግና የሣር አይነቶችም ይበቅላሉ።
በሃገራችን ውስጥ ካሉት ከሁለት ሺህ ጥንታዊያን ገዳማት መካከል የዋልድባ ገዳም መነኮሳት ከሚለዩባቸው ነገሮች አንዱ የሚለብሱት የልብስ ቀለም አይነት ነው። ሁሉም በወይባ ዛፍ ልጥ የተነከረ ቢጫ ልብስ ነው የሚለብሱት። አንድ አባት ጠይቄ እንደተረዳሁት የዋልድባ መነኮሳት ነጩን አቡጅዲድ ጨርቅ በውሃ በተፈላ የወይባ ዛፍ ልጥ እየነከሩ ወደ ቢጫነት የሚለውጡት በሁለት ምክንያት ነው።የመጀመሪያው ራሳቸውን ከአካባቢው ለማመሳስል (ከሩቅ ላለመታየት) ሲሆን ሁለተኛው ምክንያት ግን አካባቢው ወባማ በአካባቢው አጠራር «ንዳድማ» በመሆኑ በወይባ የተነከረ ጨርቅ የወባ ትንኝ ስለማይጠጋው ከወባ በሽታ ለመከላከል ስለሚረዳ ነው። ይህንን ሚስጥር ግን ብዙዎቹ አያውቁትም።
ሁለተኛው የዋልድባ ታሪካዊ ዛፍ ዲማ ነው። ዲማ እጅግ በጣም ወፍራምና ረዥም የሆነ (አንዳንዴ የዛፉ ግንድ ውፋሬ ከመለስተኛ ቤት ይበልጣል)፣ የሚበላ ፍሬ የሚያፈራ ግዙፍ የዛፍ አይነት ነው። እንደዛም ሆኖ የዛፉ ግንድ የተደራረበ ቅርፊት (ልጥ) እንጂ የሚፈለጥ፣ የሚሰነጠቅ ጠንካራ እንጨት የለውም። በመሆኑም ለቤትም ሆነ ለቁሳቁስ መሥሪያነት አያገለግልም። ይሁን እንጂ ዲማ በዋልድባ የተለየ ጠቀሜታ አለው። አባቶች ወደ ብቃት ደረጃ በሚሸጋገሩበት ግዜ ግንዱን ይቦረቡሩና (በቀላሉ ስለሚቦረቦር) ውስጥ ገብተው ቁጭ ይላሉ። በዚህ መልክ ሱባኤ የሚይዙ አባቶች በሳምንት አንዴ ብቻ ነው ቋርፍ የሚመገቡት።
ከሁሉ የሚገርመው በዚህ አይነት ሆነው (ኩርምት ብለው እንደተቀመጡ) እስከ 40 አመት በሕይወት የቆዩ አባቶችና እናቶች እንደነበሩ አስረጂው ስማቸው በክብር ተመዝግቦ መገኘቱ ነው። የዲማ አስገራሚነት ለመነኮሳቱ እንደ ቤት ሆኖ ማገልገሉ ብቻ አይደለም። አባቶች በዚህ ሁኔታ እንዳሉ ከዚህ ዓለም በሞት በሚለዩበት ጊዜ የተቦረቦረው የዛፍ ክፍል በራሱ እየሞላ ይሄድና መቃብር ይሆናቸዋል። በዚህ መልክ የቅዱሳን አፅም በሆዳቸው እንደያዙ የቆሙ በርካታ የዲማ ዛፎች አሁንም አሉ። ከዲማና ወይባ ሌላ ለተለያዩ ቁሳቁስ (መቁጠሪያ፣ መቋሚያ፣ ሙቀጫ፣ ጭልፋ፣ መስቀል. . .ወዘተ) መስሪያ የሚያገለግሉ የዕፅዋት ዓይነቶችም አሉ።
ዋልድባ በደን የተሸፈነ በመሆኑ በውስጡ ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ የዱር እንሰሳት ያለ ስጋት የሚርመሰመሱበት፣ የተለያየ ዓይነትና መጠን ያላቸው አእዋፍ የሚኖሩበት የገነት አምሳያ ቦታ ነው። አንበሳ፣ ነብር፣ አጋዘን፣ ወንድቢ(በሬ መሳይ)፣ ድኩላ፣ ሚዳቋ፣ ስስ፣ አሳማ፣ ጃርት፣ ተኩላ፣ ዥግራ፣ ቆቅ፣ ጦጣ፣ ዝንጀሮ፣ ዘንዶ፣ አዞ(ውንዝ ውስጥ) ይገኛሉ። “አንዳንዴ በዋልድባም ይዘፈናል” የሚባል ዝነኛ
አባባል አለ። ብሂሉ ከዱር እንሰሳት ጋር የተያያዘ ታሪክ ያለው ነው። ከጥንት ጀምሮ በዋልድባ ክልል ውስጥ ጥይት ተኩሶ እንሰሳ መግደል፣ በወጥመድ የዱር እንሰሳ መያዝና መግደል ፈፅሞ የተከለከለ ነው። ቢሆንም ከዋልድባ ባሻገር ያሉ ቦታዎችም በደን የተሸፈኑ ስለነበሩ አዳኞች ከሩቅ ቦታ እየመጡ በአካባቢው ያድኑ ነበር።
በተለይ ደግሞ ዝኆኖች በብዛት በክልሉ ይገኙ ስለነበር ነገስታት ሳይቀሩ ለአደን ወደ አካባቢው አዘውትረው ይመጡ ነበር። ታዲያ በዋልድባ ውስጥ ገብቶ ማደን ባይቻልም ነገስታቱና ሹማምንቱ ሰራዊታቸውን ወደ ገዳሙ ክልል በማስገባት በውስጡ ያሉትን ዝኆኖች በመረበሽ ከገዳሙ ክልል እንዲወጡ ካደረጉ በኋላ ጠብቀው ይገድሉዋቸው ነበር። ዝሆንን አድኖ ለመግደል ጊዜ ስለሚጠይቅ ነገስታቱ አደናቸውን እስኪያከናውኑ ድረስ በአካባቢው ድንኳን ተክለው ይቀመጣሉ።
በዚህ መካከል በለስ ሲቀናቸው በድንኳኖቻቸው ሆነው /ዋልድባ ድንበር/ ይሸልላሉ ፣ይዘፍናሉ፣ያዘፍናሉ። በዚህ መነሻነት ነው አንዳንዴ በዋልድባም ይዘፈናል የተባለው።
ታሪካዊ አመጣጡ –
በዋልድባ ውስጥ ሦስት ገዳማት ይገኛሉ እነርሱም ፦
1/ ዋልድባ አብረንታንት
2/ ዋልድባ ድልሽህ
3/ ዋልድባ ስቋር ይባላሉ።
ከእነዚህ መካከል ትልቁና አንጋፋው ዋልድባ አብረንታንት ነው። ይህ ገዳም(በገዳምነት በይፋ የተቋቋመው በ1398 አ.ም ) ሲሆን ከ485 አ.ም ጀምሮ ግን መናንያን በቦታው ይኖሩ እንደነበር ይታመናል። ዋልድባ ድልሽህና ዋልድባ ሰቋር ግን በቅደም ተከተል በ1505 አ.ም እና በ1658 አ.ም ነው የተመሰረቱት። በዋናው አብረንታንት ገዳምና በሁለቱ መካከል ያለው ርቀትም ቢሆን ትልቅ ነው። ለምሳሌ ያህል ከዋልድባ አብረንታንት እስከ ዳልሽህ ያለው ርቀት 50 ኪ.ሜ ይሆናል። ዋልድባ ከስፋቱ በተጨማሪ በበርካታ አስደናቂ ነገሮች ከሌሎች ገዳማት ይለያል። የዋልድባ መነኮሳት በልብሳቸው ብቻ ሳይሆን በአመጋገባቸውም ይለያሉ። ገዳማውያኑ የጣመና የላመ ምግብ ብቻ ሳይሆን ከሙዝ፣ ከተልባ፣ ከጨውና ከኑግ በስተቀር የእህል ዘር አይመገቡም። ከሙዝና ከኑግ የሚሠራውን መብል “ቋርፍ” ይሉታል።
በዋልድባ ከሙዝና ከኑግ የተሰራ የቋርፍ ምግብ መብላት የተጀመረው ከ1566 ዓ.ም. ጀምሮ ነው። ከዛ በፊት መናኒያኑ ይመገቡት የነበረው ጣብሌ፣ ገመሎና ሳዳ ከተባሉ ዕፅዋት ስር የሚዘጋጅ መራራና ጎምዛዛ ቋርፍ ነበር።
በነገራችን ላይ ሙዙን የሚመገቡት ገና ሳይበስል በጥሬው እያለ በመቁረጥና በመቀቀል ነው። ሙዙን ቀቅለውና በቋንጣ መልክ አዘጋጅተው ያስቀምጡታል። በዚህ መልክ በጥንቃቄ የተዘጋጀው የሙዝ ቋንጣ ሳይበላሽ እስከ ሰባት ዓመት ይቆያል። በዋልድባ ቀደም ሲል ከተጠቀሱት አራት ትላልቅ ወንዞች በተጨማሪ ሙዝ የሚመረትባቸው 30 ወንዞችና ምንጮች ይገኛሉ። በእነዚህ ቦታዎች እንደ ልማት ቦታው ስፋት መነኮሳት ተመድበው የመስኖ ሥራና ንብ የማነብን ተግባር ያከናውናሉ። በዋልድባ በመስኖ ስራ የተሰማራ መነኩሴ “ወንዘኛ” ይባላል። በዋልድባ ማር የሚመረት ቢሆንም (ያውም ምርጥ ማር) መነኮሳቱ አይጠቀሙበትም (አይመገቡትም) ፤ ለገበያ ወጥቶም አይሸጥም። ይልቅስ የበሰለ ሙዝና ማር ገዳሙን ለመሳለም ለሚመጡ እንግዶች (ምእመናን) ብቻ ነው የሚሰጥ። ያም ሆኖ ግን በዕድሜና በስራ ምክንያት ደክመው ለተኙ መናንያን ከድቁስ ጋር ተበጥብጦ የሚሰጥበት ጊዜ አለ። በሰሙ ግን ጧፍ በማዘጋጀት ከራሳቸው አልፈው ለሌሎችም ይተርፋሉ።
በሌሎች የኢትዮጵያ ገዳማት የማይገኝና የዋልድባ ብቸኛ መለያ ከሆኑት አንዱ ‘ስምረት’ የሚባለው ሥርዓት ነው። ስምረት ባጭሩ የሳሙኤል ልጅነት የሚገኝበት ሥርዓት ማለት ነው።(አቡነ ሳሙኤል የመጀመሪያው የገዳሙ አበመኔትና ጻድቅ ናቸው።) እንደ ምንኩስና ሁሉ ስምረት በከባድ ጸሎትና ስግደት የታጀበ የራሱ የሆነ ሥርዓት አለው። ይሁን እንጂ በዓመት ውስጥ ሥርዓተ ስምረት የሚፈፀምባቸው ቀናት የተወሰኑ ናቸው። እነዚህ ቀናትም ለወንድ ሐምሌ 5 ቀን ሲሆን ለሴቶች ደግሞ የካቲት 16 ቀን ናቸው። ይሁንና እንደ አጋጣሚ ሐምሌ 5 ቀን ረቡዕወይም አርብ ከዋለ የወንዶቹም በየካቲት ይከወናል።
ሴት መነኮሳይት ወደ ቤተ መቅደስ (ገዳሙ ውስጥ) መግባት ስለማይችሉ ሥርዓቱ የሚፈጸምላቸው ከዮርዳኖስ ወንዝ አጠገብ (ማየ ዮርዳኖስ ሳይሻገሩ) ካለው ቦታ ነው። ቡራኬ ለመቀበልም ሆነ ለማስቀደስ ሲፈልጉ ከቤተ መቅደሱ 300 ሜትር ያህል ርቀት ላይ ቆመው ነው የሚያስቀድሱት። በተረፈ ወደ ገዳሙ ለመምጣት ለማይችሉ አንዳንዴም ለማይፈልጉ መነኮሳትና መነኮሳይት ማይለበጣ እና አባ ነፃ እየተባሉ ከሚጠሩ ስዕል ቤቶች ሥርዓቱ ይፈፀምላቸዋል። ስዕል ቤት
የሚባለው ታቦተ ህግ የሌለበት ማህበረ መነኮሳቱ በጋራም ሆነ በግል ፀሎት የሚያደርጉበት የተለየ ቤት ማለት ነው።
ሴት መነኮሳይት በዋልድባ መኖር የማይፈቀድላቸው ቢሆንም ከገዳሙ ክልል ውጪ ለሴቶች ተብለው የተዘጋጁ ቦታዎች አሉ። እነርሱም ጉብታ፣ ማይ፣ ሐርገፅ(የአዞ ወንዝ) እና ቤት ሞሎ ይባላሉ። በዐጼ ባካፋ ዘመን የወልቃይትና የጠገዴ ባላባትና ገዢ የነበሩት ደጃዝማች አያና እግዚእ ያሰሩት ታሪካዊ ግንብ የሚገኘው ከሶስቱ የሴት መነኮሳይት መኖሪያ አንዱ በሆነው በሞሌ ነው።
ቀደም ሲል በገዳሙ የተለያዩ የዱር እንሰሳት እንደሚገኙ ገልጫለሁ። በዋልድባ ደግሞ በገዳማቱና ቤተ መቅደሶች ዙሪያ ከሚኖሩ መነኮሳት ይልቅ በግላቸው በየጫካው በፅሞና የሚኖሩ በቁጥር ይበልጣሉ። እንደዛም ሆኖ የዱር እንሰሳቱ (አውሬዎቹ) ስምረት የገባ መነኩሴን ፈጽሞ አይተናኮሉም። መነኮሳቱም ቢሆኑ አደጋ ያደርሱብናል ብለው አይሰጉም። አንድ የከብት እረኛ በከብቶች መካከል ያለስጋት እንደሚያልፍ ሁሉ መነኮሳቱም በነጻነት በአንበሳና በነብር መንጋ መካከል ይዘዋወራሉ። የተኛ ዘንዶም ተሻግረው ይሄዳሉ።
አባቶች እንዳወጉኝ ከሆነ አልፎ አልፎ (ለፈተና) አንበሳ መነኩሴውን የሚያልፉበትን መንገድ ጠብቆ ከመንገድ መካከል በመተኛት አላሳልፍም የሚልበት አጋጣሚ አለ። በዚህን ጊዜ መነኩሴው ሥርዓተ ስምረት በሚቀበሉበት ወቅት የተገለጸላቸውን ልዩ ቃል መጠቀም ይኖርባቸዋል። የዚህ ዓይነት ሁኔታ የገጠማቸው መነኩሴ “ግፍአ አበው” ሲሉ አንበሳው ጅራቱን እንደ ለማዳ ውሻ እየወዘወዘ ተነስቶ ይለቅለታል። ግፍአ አበው ወደ አማርኛ ሲመለስ “በአባቶች አምላክ” እንደ ማለት ነው።
በተረፈ በዋልድባ የስምረት ሥርዓት ያልተፈፀመለት መነኩሴ (ጳጳስም ቢሆን) ማየ ዮርዳኖስ አይቀዳም። በገዳሙ አይቀድስም። አይቆርብም። ቢሞትም ከአበው መቃብር አይቀበርም። እንግዲህ የዋልድባ ገጽታ ከሞላ ጎደል ይህን ይመስላል። የአይነኬነቱ መሠረቶች፣ የአይደፈሬነቱ ምስክሮች እኒህ ናቸው። የአነጋጋሪነቱ ዓይነተኛ ምክንያትም ይህ ፍጹም የሆነው መንፈሳዊነቱና ታሪካዊነቱ ነው።
ይቆየን።