Feeds:
Posts
Comments

Archive for May, 2012

ባሳለፍነው ሳምንት ማኅበረ ቅዱሳን በዋልድባ ገዳም ህልውናን ያናጋል የተባለው የስኳር ልማት ፕሮጀክት ላይ በላካቸው ልኡካን ቡድኖች አማካኝነት ያዩትንና የተመለከቱትን ፤ የእነርሱን እይታ ጨምረው የ9 ገጽ ሪፖርት ማቅረባቸው ይታወቃል ፤  በመጀመሪያ በዚህ ጊዜ ከቤተ ክርስትያኗ ጎን በመቆም የነበረውን ብዥታ ለማጥራት ጊዜ በመውሰድ በዋልድባ አካባቢ ያለውን እውነታ ለማቀመጥ ለደከሙ ወንድሞች አድናቆቴን ማቅረብ እወዳለሁ ፤ በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ መናገርም ሆነ አለመናገር የሚያስጠይቅበት ወቅት ላይ አቅም በፈቀደ መጠን ሪፖርቱ የሚያመጣውን የወደፊት ተግዳሮት ግምት ውስጥ በማገባት ይህን ስራ መስራት መቻል ከኃላፊነትም በላይ መሆኑን ላስገነዝብ እወዳለሁ ፤ ቤተክህነቱ ምዕመኑን አንገት ያስደፋ ሪፖርት ስሙኝ በማለት የኢቲቪ ጋዜጠኞችን ጠርቶ ቢያቀርብም እንኳን አሁን ደግሞ ግልጽ ያለ ነገር ምዕመኑ ማወቅ ችሏል ፤ ይህን ሪፖርት ያስቀመጣቸውን ጥሬ ሀቆች ፤ አጠይሞ ያስቀመጠውን እና የጥናቱን ውስንነት ለመዳሰስ እንወዳለን፡፡

1.      ጥናቱ ያስገኛቸው ጥሬ ሀቆች(Real Facts)
·        መንግስት በአደባባይ የዋሻቸውን ነገሮች እውነታውን ማሳየት ችሏል ፤ ለምሳሌ 16.6 ሔክታር ቦታ ከገዳሙ እንደሚነካ በማያሻማ መልኩ አስቀምጧል፡፡
·        አጽመ ቅዱሳን መነሳቱን መናገር ችሏል
·        500 ሜትር ያህል መንገድ መቀደዱ፡- የመንግስት መገናኛ ብዙሀን ከስኳር ሚኒስትሩ ጋር በመሆን ለውሸት የተፈበረኩ እስኪመስል ድረስ የአየር ሰዓት ይዘው ሲዋሹ ምንም አይመስላቸውም ፤ ‹‹አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ›› እንደሚባለው ፤ እውነታን እያዛቡ ማቅረብ ስራቸው አድርገውት ሰንብተዋል ፤ ማህበረ ቅዱሳን ያወጣው ሪፖርት መንግስት በኢቲቪ አማካኝነት የገዳሙን ቦታ አላረስኩም ሲል የገዳሙ መነኮሳት ደግሞ ታርሷል እያሉ የተወዛገቡበትን ቦታ ሪፖርቱ መታረሱን አስረግጦ በአይን እማኞች አረጋግጦልናል ፤ በጊዜው መንግስት የገዳሙን አባቶች አንድ ቦታ ላይ ስብሰባ ጠርቷቸው ነበር ፤ የገዳሙ አባቶች ግን የታረሰው ቦታ ላይ ካልሆነ አንሰበሰብም ማለታቸው ይታወቃል ፤
·        ሶስት አብያተክርስትያናት ይፈርሳሉ፡- ማይ ሐርገፅ ጊዮርጊስ ፤ ዕጣኖ ማርያም እና ማይጋባ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስትያናትን ይፈርሳሉ ብሎናል ፡፡ ከተለያየ ሚዲያ የሰማነው የሚፈርሱት የቤተክርስትያን ቁጥሮች ቢለያዩም ማህበረ ቅዱሳን የሰራው ሪፖርት ግን ሶስት አብያተክርስትያናት በትክክል እንደሚፈርሱ አስረግጦ ነግሮናል፡፡
o   እንደሚታወቀው ዋልድባ ላይ ከቋርፍ ውጪ የሚመገቡት ምግብ የለም ፤ እነዚህ ይፈርሳሉ የተባሉት ቤተክርስትያናት በዓመት ሁለት ጊዜ የዋልድባ አባቶች በዓላቸውን የሚያከብሩበት ከቋርፍ ውጪ ምግብ የሚበሉባቸው ቦታዎች ናቸው
o   መነኮሳቱ የራሳቸውን እና የገዳሙን ፍጆታ የሚውል ሰሊጥ ፤ ኑግና የመሳሰሉት የቅባት እህል የሚመረትባቸው አብያተክርስትያናት ናቸው፡፡
o    ገዳማውያኑ ሲታመሙ ፤ በእድሜ የገፉ አረጋውያን አባቶችና ጤናቸው የታወኩ መነኮሳት  የሚያርፉበትና ድጋፍ የሚደረግላቸው ቦታዎች ናቸው ፡፡ ስለዚህ እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ነገሮችን የማህበሩ ሪፖርት እውነታውን ፍንትው አድርጎ ያስቀመጠ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
2. ጠይመው የተቀመጡ
የማህበሩ አጥኚ ቡድን የአባቶችን ፍራቻ ካስቀመጠ በኋላ በስተመጨረሻ ‹‹በዚህ ፕሮጀክት ትግበራ ላይም በተጓዳኝ የታዩ ስህተቶች ወይም ጉድለቶች ናቸው›› ብሎ ሁለት ነጥቦችን አስቀጧል ፤ ሁለተኛው ነጥብ ጠይሟል ፤ እንዲህ ይላል ‹‹ችግሩን ለመፍታት የተከሄደበት መንገድ አግባብነት ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑ ይጠቀሳሉ››፡፡ መንግስት ችግሩን ለመፍታት የሄደበት መንገድ ፍጹም ስህተት መሆኑን ከመግለጽ በመቆጠብ ለስለስ ብላ ፈዘዝ ያለ ቀለም የተቀባጭ ሀሳብ ሪፖርቱ ላይ እናገኛለን፡፡
እኛ ግን እስኪ መንግስት ይህን ችግር ለመፍታ የሄደበትን የስህተት ጎዳና እንጠቁማችሁ ፡፡ ሲጀመር ይህ ጉዳይ ወደ አዲስ አበባ ይዘው የመጡትን አባቶች በስድብ መቀበል እና በማስደንበር ስህተቱ መንግስት ይጀምራል ፤ ‹‹እናንተ ደፋሮች የአንድን ሀገር መሪ ለማናገር መጣችሁ›› በማለት የስልክ መልስ ተሰቷቸዋል ፤ መነኮሳቱ ግን የመጡበትን አላማ ሳናሳካ አንመለስም በማለት ፓትርያርክ ጽ/ቤት ግልባጭ በማስገባት ዋናውን መልዕክት ለጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ በአስቸኳይ መልእክት መላካቸው ይታወቃል ፤ ይህን አድርገው ሲያበቁ በተወካያቸው መነኩሴ አማካኝነት በኩል ከቪኦኤ ጋር ቃለ መጠይቅ በማድረግ ጉዳዩን የአደባባይ ሚስጥር እንዲሆን አደረጉ ፤ ይህን ጊዜ ነበር መንግስት የተሰማውን ወሬ ውሽት ነው በማለት የስኳር ሚኒስትር ሀላፊውን አቶ አቦይ ጸሀዬን ይዞ የኢቲቪ የ2 ሰዓት ፕሮግራም ላይ አቅርቦ በዚህ እድሜያቸው እንዲዋሹ ያደረገው ፤ ቃለ መጠይቅ ያደረጉትንም አባት የት እንደሚገኙ የገዳሙ አባቶች እንዲጠቁሙ ቁም ስቅላቸውን ሲያሳያቸው የከረመው፡፡ ይህ የስህተት መንገድ በማይረቡት የቤተክህነት ሰዎች አማካኝነት እንዲረጋገጥለት በመፈለግ ቤተክህነቷ ሰዎችን ልካ የግድቡ ግንባታ ምንም ችግር እንደሌለው እንድትመሰክር የማድረግ ስራ አሰርቷል ፤ ጨምረውም እነዚህ የተላኩ ሰዎች በሪፖርታቸው ‹‹መነኮሳቱ ግድቡ ካለቀ አሳ ማጥመድ ይችላሉ›› በማለት መንግስትን ደስ የሚያሰኝ ሪፖርት አቅርበዋል ፤ ይህም ሌላኛው ችግሩን ለመፍታት የተሄደበት የስህተት መንገድ ነው ፤ ቀጥሎም የቤተክህነት ሰዎች እና ጥቂት ለስጋቸው የቆሙ መነኮሳትን ከየት እንዳመጣቸው የማይታወቁ ፤ ለጊዜው በጉዳዩ ላይ የማይመለከታቸውን የእስልምና እምነት አባቶችን አንድ ላይ ሰብስቦ ‹‹ግድቡ ገዳሙ ላይ የሚያመጣው ችግር የለም›› ብሎ ቃለ ጉባኤ በመጻፍ እና በማስፈረም ፤ ባለ ስድስት ነጥብ አቋም በማውጣት የምንጊዜም ምርጥ የኢቲቪን ድራማ ዋልድባ ድረስ ሄደው ሰርተው ለተከታታይ 3 ቀናት በቀን ሁለት ጊዜ በ3 ቀን 6 ጊዜ አቅርበውት መፍትሄ ለመሻት ሞክረው ነበር ፤ ይህም ግን የተሳካ አካሄድ አልነበረም ፤ ይህም አልበቃ ሲላቸው በትግረኛ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ላይ ፕሮግራም ሰርተውለት የሚሰራውን ስራ ህዝቡ እንዲያውቅ የማድረግ ስራ ሰርተዋል ፤ 
ይህም አመርቂ ስላልሆነ ጎንደር ከፍተኛ የኢህአዴግ ባለስልጣናት ስብሰባ አካሂደው ያለ መፍትሄ መበተኑ ሌላኛው መንገድ ነው ፤ እዚህ ስብሰባ ላይ አንድ የቤተክህነቱ ተወካይ አቶ ተስፋዬ በፊት የኢህአዴግ ሰላይ ሰው ለጎንደር ህዝብ ስለ ዋድባ ማስረዳት ሞክሮ ነበር ፤ በስተመጨረሻ የጎንደር ህዝብ ‹‹ዝም በል አንተ ነህ ስለ ዋልድባ ለጎንደር ህዝብ ማስረዳት የምትሞክረው? ›› ተብሎ የሚናገረውን ህዝብ እንዲያውቅ በስብሰባ ላይ ተነግሮታል ፤ ይህ ሰው በዚህ የስብሰባ አዳራሽ ላይ ‹‹ስኳር ተወዷል ፤ ህዝቡ እየተቸገረ ነው ፤ ምን ችግር አለ ፕሮጀክቱ ቢሰራ? ››  ማለቱም የወራት ትውስታችን ነው ፤ በስተመጨረሻ መንግስት ግራ ሲገባው የደርግ ርዝራዥ ወታደሮች ናቸው በማለት ገዳማውያኑን ከፖለቲካ ጋር የማያያዝ እና ማህበረሰቡ እንክ እንትፍ ብሎ እንዲተፋቸው የማድረግ ስራ ሰርቷል ነገር ግን አልተሳካም ፤ ይህን ሁሉ ሲያደርግ ምዕመኑ ውስጥ ውስጡን መረጃው እየደረሰው እና እየተደረገ ያለው ነገር እየገባው መጣ፡፡ ከዚያ ነገሮች እየከረሩ ሲመጡ የተቃወሙትን ሰዎች ‹‹አሸባሪ›› ከማለት ይልቅ ብሎ በማሰብ ‹‹ሀይማኖትን ሽፋን በማድረግ የፖለቲካ አቋማቸውን ለማራመድ የሚፈልጉ ሰዎች ›› በማለት ስም የመለጠፍ ስራ በመስራት የእሱን እውነተኝነት የማረጋገጥ ስራ አከናወነ ይህም አልተሳካም ፤ በስተመጨረሻ ግራ ሲገባው እንደ ሌባ በለሊት የራሱን ሰዎች በማሰማራት መረጃ ፍለጋ የገዳሙን 65 ሺህ አካባቢ የሚገመት ገንዘብ ዘረፈ እጅጉንም አባቶች አቋማቸውን እንዲለውጡ የማስፈራራት ስራ አካሄደ ፤ አሁንም የተገኝ ውጤት የለም  ፡፡
በስተመጨረሻ ከጎንደርና ከአካባቢው በሺህ የሚቆጠር ምዕመን ወደ ወልቃይት የስኳር ፕሮጀክት ስፍራ  አካፋ ፤ ዶማ ፤ ጦር ይዞ ሲነጉድ የዛኔ ‹‹ቆይ ረጋ በሉ በጠረጴዛ ዙሪያ እንነጋገር ፤ መፍትሄ ይኖረዋል›› በማለት እየሄደ ያለው መንገድ ወዴት እንደሚወስደው ተመልክቶ ያበጠ ልቡ ትንሽ ተንፈስ አለለት ፤ ይህን መንገድ ነው የማህበረ ቅዱሳን አጥኚ ቡድን ‹‹ችግሩን ለመፍታት የተሄደበት መንገድ የአግባብነት ጥያቄ የሚያስነሳ ›› በማለት የጠየመ ጽሁፍ በሪፖርቱ ላይ ያካተተው፡፡  ይህን መናገር ወይም አለመናገር ተገቢ ነበር ፤
3.     የጥናቱ ውስንነት
1.      ሪፖርቱ ሲጀምር ‹‹ካለፉት ከሁለትና ከሶስት ወራት በፊት ከዋድባ ገዳም ጋር በተያያዘ መንግስትና በገዳሙ መካከል አለመግባባት ተከስቷል›› በማለት ይጀምራል ፡፡ ከመጋቢት 25-30 2004 ዓ.ም ድረስ 5 የሚያህሉ የማህበረ ቅዱሳን አባላትን እውነታውን ለማጣራት የልኡካን ቡድን አባላቱን ወደ ቦታው እንደላከ ያስረዳል ፤ እዚህ ላይ መነሳት ያለበት መሰረታዊ ጥያቄ ቢኖር የጥናት ቡድኑ የምን አይነት ሙያ ባለቤት እንደሆኑ የተገለጸ ነገር አለመኖሩ ነው  ፤ ቡድኑ ይህን የሚያህል ትልቅ የስኳር ፕሮጀክት ገዳሙ ላይ የሚያሳድረውን ቀጥተኛም ሆነ ተዘዋዋሪ ጉዳቶችን የማውጣት ብቃቱ ምን ያህል ነው ? ፤ ይህ የጥናት ቡድን የሙያ ስብጥራቸው ምን ይመስላል ? እንደእኛ ሀሳብ በተለይ የዚህ ቡድን አባላት  በምህንድስና ትምህርት የተማሩ በሙያውም የረዥም ጊዜ ልምድ ከሌላቸው መንግስት የሚሰራውን ስራ እና ፕሮጀክቱን የመገምገም ብቃታቸው ጥያቄ ምልክት ውስጥ የሚገባ ይመስለናል፡፡ የሚያቀርቡትንም ሪፖርት ለመቀበል አዳጋች ይሆንብናል ፡፡ ለዚህ እንደ ማሳያ ለማንሳት ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ለምትሰራው ግድብ ሱዳንና ግብጽ የሚሰራውን ፕሮጀክቱ ሀገራቸው ላይ የሚያሳድረውን ተጽህኖ ለመገምገም  በዓለም አቀፍ ደረጃ በሙያው ላይ በርካታ ዓመታትን ያሳለፉና የመመዘን ብቃት ያላቸውን ባለሙያዎች  በማካተት የሚገኝውን ጥቅምና የሚያመጣው ጉዳት  የማጥናት ስራ መጀመራቸው ይታወቃል፡፡ እነርሱ በሀገራቸው በቂ  በምህንድስና የተማረ ሰው አጥተው ሳይሆን የተሻለ ውጤት ያለው የጥናት ውጤት ማግኝት በመፈለጋቸው ነው ይህን ሊያደርጉ የቻሉት ፡፡ አሁንም ማህበረ ቅዱሳን መጀመሪያ ልኡካን ቡድኑን ከመላኩ በፊት  ይህን ማየት መቻል ያለበት ከመሆኑም በተጨማሪ የሰዎቹን የትምህርትም ሆነ የስራ ሙያ ብቃታቸውን ግልጽ አድርጎ ማስቀመጥ መቻል አለበት ብለን እናምናለን ፤ የማህበሩ አባላት ሆነው ይህን ስራ መስራት የሚችሉ ባለሙያዎች ካሉ መልካም ፤ ካልሆነ ሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጭ ያሉ ባለሙያዎችን በማማከር ጊዜ ወስዶ ጥናቱን ቢያሰራ መልካ ነበር የሚል አስተያየት አለን፡፡ የ8 ቢሊየን ብር ፕሮጀክትን ገምግሞ ሪፖርት ማቅረብ  ከተለያዩ ባለሙያዎች ስብጥር ካልሆነ ከበድ የሚል ይመስለናል፡፡ የተላኩት ሰዎች ያላቸው የትምህርት ደረጃ ምንድነው? ሪፖርቱ የልኡካኑን ማንነት ባይገልጽ እንኳን የትምህርት ደረጃቸውንና ከዚህ በፊት ስለሰሩት ስራ ጥቂት ማለት ነበረበት ፤ ይህንንም ፕሮጀክት የመገምገም ብቃታቸውን ሲጀምር ማስቀመጥ ነበረበት ብለን እናምናለን፡፡ ፕሮጀክት በባለሙያዎች ቢጠና ሪፖርቱ በመንግስት ዘንድ ተዓማኒነቱ የጎላ ይሆናል ፡፡
2.     ሪፖርቱን ያቀረቡት ሰዎች ስራውን ሲጀምሩ ከመንግስት አካላትና የተሰጣቸውን መረጃ መቶ በመቶ በማመን ነው የጥናቱን ስራ መስራት የጀመሩት ፤ አምኖ መጀመር ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ፤ የተሰጣቸው መረጃ ትክክለኛነቱን በምን ማረጋገጥ ቻሉ ?
3.     የልኡኩ አላማ የሚታዩ ችግሮችን ብቻ ለመመስከር የሄደ ነው የሚመስለው ፡- ይህ ደግሞ ፕሮጀክቱ እየተሰራ ሳለ ይሁን ተሰርቶ ሲያልቅ የሚመጣውን ለውጥ ግምት ውስጥ ያስገባ ስራ መስራት እንዳይችሉ አድርጓቸዋል፡፡
4.    የጥናት ቡድኑ ፕሮጀክቱ ከተሰራ በኋላ የሚያመጣውን ተጽህኖ (Project Overall impact) ማሳየት አልቻሉም
a.   About   Urbanization ?
b.    መንፈሳዊ ህይወት ላይ የሚያመጣውን ችግር
c.     ስነ ምህዳር ተጽህኖ ፡- ይህ ፕሮጀክት ተሰርቶ ቢያልቅ አሁን የምናውቀው ክብረ ገዳማት ዋልድባ ስነ-ምህዳሩ ሳይቀየር  ይኖራል ?
d.     ፕሮጀክቱ ብህውትናው ህይወት ላይ የሚያመጣውን ችግር
e.     የአባቶቻችን የተመስጦ ህይወት ምን ሊመስል ይችላል ? የሚሉትን ጉዳዮች መመልት አልቻለም
5.     የተነሱበት የጥናት ወሰን (scope) በጣም ጠባብ በመሆኑ በፕሮጀክቱ ላይ አስፍቶ ያለመመልከት ችግር ይታያል ፤
6.    የመጀመሪያው ገጽ ላይ ጥናቱን ሲያካሂዱ የገዳሙን አባቶች ፤ የፕሮጀክቱን ኃላፊዎች እና የተለያዩ የማህበረሰቡን ክፍሎች ሀሳብ እንደያዘ ያስረዳል ፤ እዚህ ላይ ግን እነዚህ አካላት ብቻ መሰረት አድርጎ ጥናት ማካሄድ ጥናቱን ሙሉ ያደርገዋል የሚል እምነት የለንም ፤ ቢያንስ በየስልጣን ተዋረዱ የሚገኙ የመንግስት ባለስልጣኖችን ታሳቢ ማድረግ ይገባዋል ብለን እናምናለን፡፡ ፕሮጀክቱን ካዘጋጀው አካል ጀምሮ ፕሮጀክቱን በኃላፊነት ወስዶ እስከሚያስፈጽመው አካል ድረስ ፤
7.     መንግስት ስራውን ከጀመረ አንስቶ እስከ አሁን ድረስ የሰራውን ስራ አይገልጽም ፤ እስከ አሁን ምዕመኑም ሆነ የገዳሙ አባቶች ያሳለፉትን ውጣ ውረድ አይዳስስም ፤ መንግስት በመገናኛ ብዙሀን የተናገራቸውን ነገሮች የአጥኚ ቡድኑ በአካል ሄዶ የተመለከተውን ነገር በንጽጽር ለማቅረብ አይሞክርም ፤ መንግስት እያካሄደ ያለውን ተግባር ገዳሙ ውስጥ የሚገኙት አባቶች ምን ያህል ጉዳት ይድረስባቸው ፤ አይድረስባቸው ለመናገር አይደፍርም ፡፡
8.    ይህን ጥናት ማህበረ ቅዱሳን ብቻ ባያጠናው መልካም ነበር ፤ የስኳር ልማቱ በገዳሙ ላይ የሚያደርሰው ጉዳት መጀመሪያ የሚመለከታት የኢትዮጵያ ኦርዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ገዳማትና አድባራት መምሪያ ነው ፤ ነገር ግን ጉዳቱ ሳይታያቸው ቀርቶ ሳይሆን ጉዳዩን ቤተክህነታችን አይቶ ዝም ቢል ማህበረ ቅዱሳን ቦታው ድረስ ሄዶ መመልከት መቻሉ እና የአቅሙን ሪፖርት ማቅረቡ ሊያስመሰግነው ይገባል ፤ ይህ ነገር መልካም ቢሆንም የተሻለ ጥናት ለማድረግ ከመንግስት እውቅና እስከተሰጠው ድረስ ከተለያዩ የመንግስት አካላት ማለትም  ፤ ከባህልና ቱሪዝም ቋሚ ኮሚቴ አባላት(የህዝብ ተመራጮች) ፤  ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ከተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ፤ ከአማራ እና ከትግራይ ክልል ባለስልጣናት ፤ ከከፍተኛ የሀይማኖት አባቶች ፤ ከታዋቂ ሰዎች ፤ ግድብ ስራ ከሚሰሩ ከባለሙያዎች(Engineers) ፤ ከዩኒቨርሲቲ መምህራን ፤ ፕሮጀክቱን ከቀረጹት ባለሙያዎች ፤ ፕሮጀክቱን ከሚያስፈጽሙት ሰዎች በተዋቀረ ኮሚቴ ጥናቱ ረዘም ያለ ጊዜ ተወስዶ ቢካሄድ የጥናቱ ተቀባይነቱ በመንግስት የጎላ ይሆናል የሚል አመለካከት አለን ፤ ያለበለዚያ ግን እንከን የማይወጣለት ንጹህ ስራ መስራት ቢቻል እንኳ ማህበረ ቅዱሳን ያቀረበውን ሪፖርት በቤተክህነቱም ሆነ በመንግሰት ዘንድ ተቀባይነቱ ላይ ጥያቄ ይጭራል፡፡
9.    አቶ አባይ ጸሀዬ ፓርላማ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት መሰረት ከአካባቢው የሚነሱ ወደ 7ሺህ አባወራዎች(20 ሰዎች) እንዳሉ አስረድተዋል ፤ በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ደግሞ ጠቅላላ ነዋሪዎቹ በቁጥር 20 ሺህ እንደሚደርሱ ዘግቧል ፤ የጥናት ቡድኑ እነዚህን አስመልክቶ ከኢንጅነር ይስሀቅ እንደተረዳው እነዚህ ሰዎች የት እንደሚሰፍሩ ግልጽ ሆኖ የተቀመጠ ነገር እንደሌለው በመላምት የተነገራቸውን በመላምት አስቀምጠውታል ፤ ጥናትን ለማቅረብ ደግሞ ደግሞ የሚጨበጥ ነገር መኖር አለበት ፤ ይህን የሚያህል ፕሮጀክት ላይ የእነዚህ ሰዎች ማረፊያ ታሳቢ ሳይደረግ የተሰራ ነው ለማለት ይከብዳል ፤ ሚኒስትሩም የነዋሪዎች ማረፊያ መሰረተ ልማት ችግር እንደፈጠረባቸው ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት የ9 ወር የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ገልጸዋል ፤ እዚህ ላይ ከኢንጅነሩ ፤ ከጥናት ቡድኑ እና ፕሮጀክቱ መሀል ክፍተት ያለበት ይመስለናል፡፡ የስኳር ፕሮጀክቱ ሙሉ ጥናት የአጥኝው ልኡካን ቡድን ጋር እጁ ላይ እንደገባ እርግጠኛ ሆነን መናገር አያስችለንም  ፤ ለምን ቢባል ? መላምት የማያስፈልጋቸው ነገሮች በመላምት የተቀመጡበት ሁኔታ ሪፖርቱ ላይ ይታያል፡፡  በዚህ ምክንያት የጥናቱ ሙሉ ሰነድ እጃቸው ላይ መግባት መቻሉን ጥያቄ ይጭራል ፤ በሪፖርተር ጋዜጣ እንዳነብነው አባይ ጸሀዬ ሲናገሩ እንደሰማነው ነዋሪዎቹ ሲነሱ አብረዋቸው የሚገኙ ትምህርት ቤቶች ፤ ጤና ተቋማት እና ቤተክርስትያኖች ይነሳሉ ፤ እነዚህ አካባቢ ደግሞ 18 ቤተክርስትያናት እንደሚኖሩ ከገዳሙ አባቶች እና ከአቦይ ጸሀዬ ለማወቅ ችለናል ፤ የማህበሩ ሪፖርት ግን 3 ብቻ ብሎ ያስቀምጣቸዋል፡፡ ውሀ የሚያጥለቀልቃቸው 3 ሊሆኑ ይችላሉ የሚነሱት ማህበረሰብ ውስጥ የሚገኙት ደግሞ 15 ናቸው ፤ እነዚህን የመዳሰስ ሁኔታ በሪፖርቱ ላይ አይታይም፡፡
10.   ስለ አጽመ ቅዱሳን የቀረበው ሪፖርት ላይ ፡- የስኳር ኮርፖሬሽን ኃላፊ አቶ አቦይ ጸሀዬ 27 የሚደርሱ አጽሞች እንዳነሱ እና 20ዎቹ ባለቤት እንደተገኝላቸው በክብር እንዳለፉ በኢቲቪ ቀርበው ሲያስረዱ ነበር ፤ ሪፖርቱ ላይ ከኦፕሬሽን ኃላፊው አቶ ጌታቸው እንዳሉት ቁጥሮቹን 20 ሆነው እናገኛቸዋልን ፤ መንግስትን ከሚወክሉ ባለሙያዎችና ባለስልጣናት በአንድ ምላስ ሁለት የሚጋጭ ነገር እየሰማን ነው ፤ አቶ አባይ ጸሀዬም ሆኑ አቶ ጌታቸው መንግስትን ወክለው የሚናገሩ ይመስለናል ፤ እዚህ ላይ ለእኚህ የኦፕሬሽን ሀላፊ የአቦይ ጸሀዬ የተናገሩትን ነገር ማንሳት አልተቻለም ነበር ወይ ? ወደ ቦታው ሲሄዱ መንግስት በሬዲዮም ሆነ በቴሌቪዥን ያቀረባቸውን ዘገባዎች ጠንቅቀው ቢያውቁት እየተወራ ያለውን እና እየተሰራ ያለውን ለማነጻጸር ይረዳቸዋል የሚል አስተያየት አለ ፤  የገዳሙ አባቶች የሚሉትን ሳንጠቅስ ማለት ነው፡፡
11.     አቶ አባይ ጸሀዬ እስከ አሁን የፈረሰ አንድም ቤተክርስትያን የለም ስለሚፈርሱ ቤተክርስትያኖች ወደፊት ከእምነት አባቶች ጋር እንነጋገርበታለን ብለዋል ፤ በዚህ ላይ የተባለ ነገር የለም ፤ በዚህ ላይ እንነጋገርበታለን የተባለው ቤተክርስትያኖቹን ስለማፍረስ ሂደት ላይ ነው ወይስ ሌላ ነገር?
12.   የዚህ ፕሮጀክት ስራ ሲከናወን መንግስት የገዳሙ መነኮሳት ብሎ የሰበሰባቸው አባቶች በቴሌቪዥን ተመልክተን ነበር ፤ እነዚህ አባቶች ገዳሙን የሚወክሉ ናቸው ወይስ አይደሉም ? በሪፖርቱ ላይ የተገለጸ ነገር የለም፡፡ ፕሮጀክቱን የሚቀበሉ እና የማይቀበሉ መነኮሳት እንዳሉ እናውቃለን ፤
13.   የማህበሩ አስተያየቶች ፡- ይህ አስተያየት በጣም ያነሰ ሆኖ አግኝተነዋል ፤ ለ5 ቀናት ዋልድባ ድረስ በመሄድ ችግሩን በማጥናት አደጋውን ሙሉ በሙሉ በማይገልጽ መልኩ የተቀመጠ ይመስለናል ፤ አጥኝ ቡድኑ የራሱን አስተያየት ከመስጠት ይልቅ አባቶች እንዲህ አይነት ስጋት አላቸው እያለ የእነርሱ አንደበት ላይ አስታኮ ሪፖርን ያቀረበበት ሁኔታ ይታያል ፤ ከተለያዩ ሚዲያዎች የሰማነው የገዳሙ አባቶች ያስቀመጡት ፍራቻን በሪፖርቱ በጠቅላላ አልተዳሰሰም ፤ ወይ የገዳሙ አባቶች ትክክለኛ መረጃ አልተናገሩም ወይም ደግሞ አጥኚ ቡድኑ በፍራቻ ማቅረብን አልወደደም ፤ እውነታውን ብቻ ማቀመጥ መፍትሄ ይሆናል የሚል እምነት የለንም፡፡
14.   የሪፖርት አቀራረብ ፡- ሪፖርት አቀራረቡ ደረጃውን የጠበቀ አይደለም ፤ ሪፖርቱ ማካተት ከሚገባቸው ነገሮች በቅደም ተከተል መከተል ይገባው ነበር ፤
a.     ስለ ዋልድባ ትንሽ መግቢያ፤(ለ9 ገጽ ሪፖርተ 3 ገጽ መግቢያ መቅረብ የለበትም)
b.    መንግስት ስለሰራው ስራ ፤- መንግስት እስከ አሁን በገዳሙ አካባቢ ምን አይነት ስራ አከናወነ ፤ አሁንስ ምን እየሰራ ይገኛል ፤ በቦታው ላይ ስለተሰሩት ካምፖች ፤  ……. ሌላም ነገሮችን
c.     በልኡካን ቡድን ውስጥ ስለተካተቱት ሰዎች ጠለቅ ያለ መረጃ (ማንነታቸውን ማወቅ ባንፈልግ እንኳን የትምህርት ደረጃቸው ፤ ከዚህ በፊት የሰሩትን ፕሮጀክት ፤ ያላቸውን የስራ ብቃት እና መሰል መረጃዎችን መገለጽ ነበረበት ፤ እነዚህ ነገሮች በግልጽ ካልተገጹ ሙያ የሌላት ሴት የሰራችው ወጥ እንዳይሆን )፤
d.     የጥናቱን አላማ እና ግቡንም ግልጽ አድርጎ ማስቀመጥ አለበት ፡- መነሻውንና መድረሻውን የሚፈለገውን ውጤት ፤ ጥናቱን የሚያካሄድበት እና ያካሄደበት መንገድ መቀመጥ መቻል አለበት..
e.      ፕሮጀክቱ ለገዳማውያን መልካምም ሆነ የሚጎዳ ነገር ካለው ጥናቱ  በግልጽ  ማስቀመጥ አለበት እንጂ የገዳሙ አባቶች እንዲህ አይነት ስጋት አለባቸው ፤ እንዲህ አይነት አደጋ ሊያጋጥመን ይችላል እያለ የጥናት ቡድኑ መናገር የፈለገውን ነገር በመናገር እውነታውን  በአባቶች ፍራቻ ላይ መሰረት አድርጎ ማስቀመጥ የለበትም ፤ ጥሬ እውነቱን ማስቀመጥ መቻል አለበት   ፡፡
f.      የጥናት ቡድኑ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ያየውን የተመከተውን ነገር ከግንዛቤ ውስጥ በማስገባት የመፍትሄ አቅጣጫ መጠቆም መቻልም አለበት ፡- ጥናት አንዱ ጥቅሙ ችግሩን አይቶ ተገቢ መፍትሄ ለመስጠት ነው ፤ እንደ እኛ ዩኒቨርሲቲዎች የመመረቂያ ጽሁፍ መደርደሪያ ላይ የሚቀመጥ መሆን መቻል የለበትም ፤ በዚህ ጊዜ ማህበረ ቅዱሳን ዋልድባ ላይ ያንዣበበውን ችግር ጥናት አድርጎ ነበር ለማለት ሳይሆን አጥንቶ የመፍትሄ ሀሳብ አቅርቦ ነበር ቢባል መልካም ነው፡፡
g.      ጥናቱ እነዚህ ነገሮች ቢስተካከሉለት የገዳማውያኑን ስጋት ያስቀራል ብሎ አማራጭ መፍትሄዎችን ማስቀመጥ መቻል  አለበት
h.    በስተመጨረሻም የጥናት ሰነድ  ሊያሟላ የሚያስፈልጋቸውን  ነገሮች ሁሉ ማሟላት አለበት ፤
15.   በማጠቃለያው ላይ ማህበሩ ያዘጋጀው ሪፖርት መንግስት አካላት ጋር ይዞ ሄዶ እንደተወያየ ይገልጻል ፤ ‹‹ምንም እንኳን ህዝቡንና መነኮሳቱን ያሳዘነ ድርጊት ቢከሰትም የተፈጠረውን ችግር በውይይት ለመፍታት በመንግስት በኩል ዝግጁነት እንዳለ ለመረዳት ችሏል›› ይላል ፡፡ ምን አይነት ችግር ነው ህዝብና መነኮሳትን ያሳዘነው ? ሪፖርቱ ምንም ሳይናገር ለማጠቃለል እና ለመደምደም ይጥራል፡፡  በመሰረቱ ማጠቃለያ ማለት ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ያለውን ሪፖርት በመጭመቅ ገላጭ በሚያስብል መልኩ ሀሳብ የሚቀርብበት አንቀጽ ነው፡፡  ነገር ግን ‹‹ህዝቡንና መነኮሳቱን ያሳዘነ ተግባር›› በግልጽ በሪፖርቱ ላይ  የቀረበበት ቦታ የለም ፤ ሪፖርቱ ላይ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ሲደረግ የነበረው እና የተደረገው ነገር ግልጽ ባለ መልኩ ሳይቀመጥ ፤ ህዝብ ያዘነበት ተግባር ፤ መነኮሳቱ የተከፉበት ምግባር ሳይጻፍ መደምደሚያው ላይ ችግሩን በውይይት ለመፍታት በመንግስት በኩል ዝግጁነት እንዳለ ይነግረናል ፤ ለምን እያንዳንዷ ነገር የመንግስት ? የህዝብ ? ወይስ የመነኮሳቱ ? ችግር እንደሆነ አልተገለጸም ፤ በስተመጨረሻ መፍትሄውን ለማስቀመጥ ብቻ ሳይሆን በ3ወራት ውስጥ የተከናወኑትን እያንዳንዷን ነገር መገለጽ ነበረበት የሚል እምነት አለን ፤ የሆነውን ካልገለጹ ደግሞ የተፈጠረውን ችግር እና መናገር የፈለጉትን  የመፍትሄ ሀሳብ አንድ ላይ መዝለል ተገቢ ነው ብለን እናምናለን፡፡
16.   በሌላ በኩል በማጠቃለያው ላይ ‹‹ፕሮጀክቱ በገዳሙ እና በገዳማውያኑ ላመጣው ጉዳት ተገቢውን ካሳና ተለዋጭ ቦታ ለመስጠት ፈቃደኛ እንደሆነም ተገንዝቧል ፤ ስለዚህም በቤተክርስትያኗ በኩል አስፈላጊው አካል ተመድቦ ውይይት እንዲጀምር በተደረገው ውይይት ተገልጿል›› በማለት ያስቀምጣል፡፡ይህ ነገር ሪፖርቱ ላይ ግልጽ አይደለም ፤ መንግስት ላረሰው የገዳሙ ይዞታ ነው ተለዋጭ ቦታ የሚሰጠው? ወይስ ይፈርሳሉ ተብለው ስለታሰቡት አብያተክርስትያናት ? መንግስት ለሰራው ወይም ለመስራ ላሰበው  ስራ የትኞቹ ናቸው ካሳ የሚያስፈልጋቸው ? ለፈነቀረው የቅዱሳን አጽም? ያለአግባብ የተንገላቱን መነኮሳት ? አልገባንም፡፡ ስለ ‹‹ካሳ›› ከተነሳ የመጀመሪያ ስራ የሚሆነው በቦታ እና በብር ካሳ የሚጠየቅባቸው እና የማይጠየቅባቸው ተብለው መለየት መቻል አለባቸው ፤ ለምን ቢባል ይህ የእምነት ጉዳይ ነው ፡፡
4. ማጠቃለያ
በአሁኑ ሰዓት ለልማት በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች የከተማዋን ደረጃ ለማሻሻል ነዋሪዎችን በማማከር የሚነሱበትን እና ቦታው የተሻለ ህንጻ የሚሰራበት ሁኔታ እየተመለከትን ነው ፤ ይህ መልካም ሆኑ ሳለ መንግስት ዋልድባን የሚያህል ክብረ ገዳማትን ግሬደር አስገብቶ ሲያርስ ቤተክርስትያኒቱን የሚወክሉትን አባቶችንና የገዳሙን መነኮሳት  አለማማከሩ እጅጉን አስገርሞናል ፤ አዲስ አበባ ላይ የአንድ ሰው ቤት ለማፍረስ ከ10 ያላነሱ የቀበሌ ስብሰባዎች ቀድመው ሲደረጉ ዋልድባን የሚያህል የቤትክርስትያናችን ዓይን ገዳምን ለማረስ ለማማከር አንድ እርምጃ አለመሄዱ መንግሰት ለእኛ ያለው የንቀቱን መጠን ያመላክተናል፡፡‹‹ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ›› ይላል ያገሬ ሰው፡፡  መንግስት ለቤተክርስትያናችን ያለው እይታ ምንም ያህል የተዛባ ቢሆንም ዋናው  ‹‹እኛ ለራሳችን የምንሰጠው እይታ እርሱ ከሚሰጠን አይነስ›› ነው ቁም ነገሩ  ፤ ማንም በሸውራራ አይኑ ይመልከተን የእሱ መመልከት የእኛን እይታ ላይ የሚፈጥረው ችግር የለም፡፡
 በተጨማሪ ግድቡ በቦታው ላይ በመሰራቱ የውሀው መጥለቅለቅ ችግር ያጋጥማል ፤  መንግስት ፕሮጀክቱ ላይ እንዳሰበው ሳይሆን ዝናብ እንደዘነበ መጠን የውሀው መጠን ከፍ ሊል ይችላል ፤ በዚህ ጊዜ ማንም የማይቆጣጠረው የሩቅ ምስራቆችን አይነት ጎርፍ ይከሰታል ፤ ብዙ መቶ አመታትን በሰላም የዘለቀ ገዳም የአንድ ቀን የጎርፍ ሲሳይ እንዳይሆን ስጋት አለን ፤ ይህ ደግሞ ለማንም አይጠቅምም ፤
እኛ መፍትሄ ብለን የምናስቀምጠው ነገር ፤ ሀገራችን ኢትዮጵያ ያላትን የውሀ ሀብት የተጠቀመችው ከ10 ከመቶ በታች ነው ፤ ስለዚህ ቀሪ 90 በመቶ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል ላይ ወንዞች እንዳሻቸው የሚፈሱበት አካባቢዎች በርካታ ናቸው ፤ ስለዚህ የቦታም ሆነ የውሀ እጥረት የሌለባት ሀገር ስለሆነች መንግስት ፕሮጀክቱን ወደ ሌላ ቦታ ያዛውረው ዘንድ ምክራችን ነው፡፡ ይህ ጉዳይ 1000 ሺህ ጊዜ ሪፖርት ቢሰራበት አሳማኝ ነገር ለማምጣት ስለሚከብድ ፕሮጀክቱ መቆም አለበት የሚል አቋም አለን፡፡ያለበለዚያ ግን ከእግዚአብሔር ጋር እንደምትገዳደሩ እወቁት ፤
በብልሀት የተሰራው ሪፖርት ከነችግሩ ጥሩ ነው ፤ አንድ አይናማ በአፈር ስለማይጫወት ሪፖርቱ ላይ ፍርሀት ፤ ብልጠት ፤ ጥንቃቄ ፤ ከመንግስትም ሆነ ከቤተክህነቱ ጋር ላለመጋጨት የተደረገ አካሄድ  መልካም ነው፡፡
ያቀረብነውን ሀሳብ ብቻ  መሰረት አድርገው አስተያየትዎን ይጻፉልን

Read Full Post »

(አንድ አድርገን ግንቦት 21 2004 ዓ.ም)፡- ከቀናት በፊት ተጀምሮ ፍጻሜውን በአስር ነጥብ የአቋም መግለጫ የተጠናቀቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ በርካታ መስተካከል የሚገባቸውን ነገሮች ለህዝበ ክርስትያን እና ለቤተክርስትያኒቱ በሚጠቅሙ አጀንዳዎች ላይ ተነጋግሮ መጠናቀቁ ይታወቃል ፤ ስብሰባው ሲጀመር የቅዱስ ሲኖዶስ 20 አጀንዳዎችን ከተቀረጹ በኋላ የዋልድባ ጉዳይ እንደ አጀንዳ አለመያዙን እያነጋገረ መሆኑን ገልጸን ጽፈን ነበር ፤ እኛ እንዳልነው ስብሰባው ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ በዋልድባ ጉዳይ ላይ ምንም የተባለ ነገር አለመኖሩ ምዕመኑን አስደምሞታል ፤ ለምን አባቶች አቋማቸውን መግለጽ አልፈለጉም ? ከዚህ በላይ ችግርስ አሁን በቤተክርስትያኒቱ ላይ አለን ? ምዕመኑ የተቃወመውን ያህል አባቶች ምን እንደሚሉ መስማት የብዙዎች ፍላጎት ነበር ፤ ነገር ግን ይህ ሲሆን መመልከት አልቻልንም ፤

ይህ ጉዳይ ሀገር ያወቀው ጸሀይ የሞቀውን ነገር እንደ አጀንዳ ይዘው መነጋገር አለመቻላቸው ብዙዎችን አስገርሟል ፤ እኛ ባለን አቋም ፕሮጀክቱን መቃወምም ሆነ መደገፍ ሁለቱም አቋም ነው የሚል እምነት አለ ፤ በኢሜል ከሚደርሱን በርካታ ጥያቄዎች አንዱ የዋልድባ ነገር ምን ደረጃ ደርሷል? የሚል ጥያቄ ነው፡፡  ፤ የነገሩን አካሄድ ስንመለከት ትንሽ ከመንግስት በኩል ለዘብ የማድረግ አዝማሚያ ይታያል ፤ ከገዳሙ አባቶች እና ከቤተክህነቷ ጋር ለመነጋገር ቀነ ቀጠሮ ባይቆርጥም ለመነጋር ሀሳብ እንዳለው ለማወቅ ተችሏል ፤ ማህበረ ቅዱሳን ይዞት የመጣው ሪፖርት ላይም ይህን የሚደግፍ ሀሳብ እንዳለ አመላክቷል ፡፡ከሳምንታት በፊት ህዝቡ ወደ ወልቃይት ስኳር ፕሮጀክት ሲወርድ እንደነበረ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሀን ቦታው ድረስ ሄደው ከመጡ ሰዎች መስማት ችለን ነበር ፤ መንግስትም ሚያዚያ 29/2004 ዓ.ም ህዝቡን ለማወያየት አስቦ ነበር ፤ ስብሰባው ይደረግ አይደረግ የታወቀ ነገር ባይኖርም ፤
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመንግስታቸውን የ9 ወር የስራ ክንውን በገለጹበትና ስለ አሸባሪነት ጠለቅ ያለ መረጃ ባተላለፉበት  ጊዜ ጀምሮ መንግስት የአካሄድ ለውጥ ማድረጉን ሁኔታዎች ያመላክታሉ ፤  በዚህ ስብሰባ ላይ እየተጋጋለ የመጣውን  የሙስሊሞች ጥያቄ ፤ የዋልድባ ገዳም የስኳር ፕሮጀክት ጉዳይ እና የህዝብ ተቃውሞ መሰረት በማድረግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልስ ይሰጡባል ተብሎ ቢጠበቅም በስተመጨረሻ ባደረጉት የአቋም ለውጥ ዝምታን መምረጣቸው ይታወቃል፡፡ ሪፖርቱ እስከሚቀርብበት ጥቂት ቀናት ድረስ ዋድባን መሰረት አድርገው ቦታው ላይ እየሆነ ያለውን እና የተደረገውን ስራ የህዝቡን ጥያቄ መሰረት በማድረግ መልስ ይሰጡበታል ፤ የመንግስታቸውን አቋም ያንጸባርቃሉ ተብሎ ቢጠበቅም ይህ ግን ሆኖ መመልከት አልቻልንም ፤ ይህ ጉዳይ ከሙስሊሞች ጥያቅ ያነሰ ሆኖ ሳይሆን በመንግስት በኩል የአካሄድ ለውጥ እንዳለ አመላካች ነው የሚልም አስተያየት አለ፡፡
በመሰረቱ ጉዳዩ የማያነጋግርና አቋም የማይወሰድበት ሆኖ ሳይሆን ከመንግስት የተንጸባረቀው የአቋም ለውጥ አባቶች ጉዳዩን በጉባኤው ላይ እንዳይነጋገሩበት መንገድ የከፈተ ይመስላል ፤ አባቶች “ለአሁን እንለፈው ወደፊት መንግስት ጉዳዩን ወደኛ ሲያመጣው እንነጋገርበታለን” የሚል አካሄድን የተከተሉ ይመስላሉ፡፡ ፤ በሌላ በኩል “መንግስት ላሰበው ፕሮጀክት ቤተክርስትያኒቱ በሲኖዶስ ደረጃ አቋም እንዳትይዝ ትንሽ ዘግየት እንድትል ትዕዛዝ የተላለፈ ይመስላል” የሚሉ አስተያየቶች ይሰማሉ ፡፡ በተጨማሪም ጉዳዩን እንዲለዝብ ያደረገው  አንዱ እና ዋንኛው ሆኖ የሚወሰደው በአካባቢው የሚገኙ አርሶ አደሮች “ይህ ሊሆን አይደለም ሊታሰብ የማይገባው ተግባር ነው ፤ በእምነታችን ላይ የመጣ የማፈራረስ ሴራ ነው” በማለት ጦር ፤ ዶማ ፤ አካፋ ይዘው ወደ ቦታው መትመማቸው መሆኑ ይታመናል ፤ ጉዳዩም ወዴት እንደሚሄድ በማህበረሰቡ ዘንድ ያለውን  መነሳሳት በመመልከት የያዘውን አቋም ለዘብ እንዲያደርግ ምክንያት ሆኗል ተብሎ ይታሰባል፡፡
 ጉዳዩ እንዳይነሳ ካደረጉት ነጥቦች ጥቂቶቹ
1.     ስፍር ቁጥር የሌላቸው የውስጥ ችግሮችን መፍታት አለመቻል፡- በዓመት ሁለት ጊዜ የሚደረገው የሲኖዶስ ስብሰባ ከጊዜ በኋላ በአቡነ ጳውሎስ አምባገነንነ አካሄድ ፤ እኔ ያልኩት ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ ጸባይ ዘወትር ለመስማት የሚታክት  ንትርክ  መስማት ጆሯችን የለመደው ነገር ሆኗል ፤ በቤተክርስያኒቱ ውስጥ ያሉት ችግሮችን ቀድሞ አለመፍታት ይህን ጉዳይ ወደ ኋላ እንዲል አድርጎታል ፤ የተሀድሶያውያንና የመናፍቃን ፤ ለህገ ቤተክርስትያን ተገዥ አለመሆን ፤ የአቡነ ጳውሎስ ረዥም እጅ ፤ ሙስና ፤ ጎጠኝነትና  አድርባይነት  የመሳሰሉት ችግሮች ቤተክርስትያኒቷ በሁለት እግሯ ቆማ ወንጌልን ለመላው ዓለም እንዳታዳርስ ፤ ይህን የመሰለውን አንገብጋቢ ጉዳይ በጊዜው እንዳትመክርበት እንቅፋት ሆኖባት ይገኛል ፤ አብዛኛው የሲኖዶስ ስብሰባ የያዘውን አጀንዳ በአግባቡ ሳይቋጭ ለሚቀጥለው እንደሚያስተላልፍ ይታወቃል ፤ ይህ ማለት የችግሩን ብዛት እና መፍትሄ የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች መበራከት ያመጣው ችግር መሆኑ እሙን ነው ፤ ስለዚህ በርካታ የውስጥ ችግር ያለባት ቤተክርስትያን በመሆኗ መጀመሪያ የውስጡን የማጥራት ስራ ስላተሰራ ጉዳዩን ወደ ኋላ እንዲል አድርጎታል፡፡

2.    ሀገር ውስጥ የሚኖረው ምዕመን ገፍቶ መሄድ አለመቻል ፡- በመሰረቱ የዋልድባ ጉዳይ ከተሰማ ጀምሮ ሰዎች በጉዳዩ ላይ አትኩሮት ሰጥተው በየጊዜው በቪኦኤ ፤ በተለያዩ ድረ ገጾችና ጋዜጣዎች ሲከታተሉ መመልከት ችለን ነበር ፤ ነገር ግን ያሰቡትንና የተሰማቸውን ጥያቄያቸውን በአንድነት ሆነው ማቅረብ የቻሉ በጣም ጥቂቶች ናቸው ፤ “ይህ ጉዳይ የገዳሙን ህልውና የሚያናጋ እና እምነታችን ላይ የተሰነዘረ ጦር ነው” በማለት በጎንደርና አካባቢው ያሉት ነዋሪዎች መንግስት የስኳር ልማት አቋቁምበታለው ብሎ ማረስ ወደ ጀመረው ቦታ በተናጠልና አነስ ባለ አንድነት መንቀሳቀሳቸው ይታወቃል ፤ ይህም ጥያቄ እዛው መቅረቱ ጉዳዩ በአባቶች ዘንድ ውሀ ደፍቶ የመነጋገሪያ አጀንዳ እንዳይሆን የራሱን አስተዋጽኦ አድርጓ ፤ በመሰረቱ ይህ ጉዳይ የተሰማ አካባቢ ስድስት ኪሎ የሚገኝው የቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስትያን አንድ እሁድ የቀድሞ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን በፌስ ቡክ አማካኝነት በጉዳዩ ላይ ለመነጋር ስብሰባ መጥራት ተችሎ ነበር ፤ ነገር ግን በወቅቱ ከተባለው ሰዓት በፊት ሲቪል የለበሱ የአዲስ አበባ ፖሊስ እና ፌደራል ፖሊስ አባላት ግቢውን እንደ አንበጣ ወረውት የሚሆነውን ነገር ለመከታተል ቀድመው በቤተክርስትያኑ ተገኝተው ነበር፡፡ ህገ-መንግስቱ አንቀጽ 30 የመሰብሰብ ፤ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግና አቤቱታ የማቅረብ መብት ላይ ንኡስ አንቀጽ 1 ላይ “ማንኛውም ሰው ከሌሎች ጋር በመሆን መሳሪያ ሳይዝ በሰላም የመሰብሰብ ፤ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ነጻነትና አቤቱታን የማቅረብ መብት አለው፡፡” በማለት በግልጽ ያስቀምጣል መንግስታችን ግን የህጎች ሁሉ የበላይ ላይ ይህን አስቀምጦ ሰዎች ለመሰብሰብ ሲሞክሩ ቀድሞ ከስብሰባው በፊት ቦታው ላይ በመገኝት ሰዎች በነጻነት ስብሰባ እንዳያደርጉ በማድረግ የሽፍታነት ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡ ሲፈልግ ደግሞ መሰብሰብ ትችላላችሁ ብሎ ህጋዊ ፍቃድ ይሰጥና ተሰብሳቢዎች መሰብሰቢያ አዳራሽ እንዳያገኙ በሮቹን ሁሉ ይቆልፋል ፤ አዳራሽ ያላቸውን ሆቴሎችንም በቀጭኗ ሽቦ ቀጭን ትዕዛዝ በማስተላለፍ ህገ መንግስቱ የፈቀደውን መብት የመጣስ ስራ ይሰራል ፤  በዚህ አይነት ምክንያቶች ስለ ዋልድባ ጉዳይ መረጃ የደረሰው ምዕመን እንዳይሰበሰብ እና በጉዳዩ ላይ ሀሳብ እንዳያንሸራሽር መንግስት እንቅፋት በመሆኑ ስብሰባ ለማድረግ አይደለም ለማሰብ አልቻለም ፤ ሀገር ውስጥ ከሚገኙ ምዕመናን ይልቅ በውጭ የሚገኙ ምዕመናን በዋልድባ ስኳር ልማት ላይ ጊዜያዊ አለማቀፋዊ ኮሚቴ አቋቁመው እየተንቀሳቀሱ መሆኑ ይታወቃል ፤ እነዚህ ወንድሞችና እህቶች June 4 2012 (ግንቦት 27 2004 ዓ.ም) እስከ ዛሬ ተደርጎ በማይታወቅ መልኩ በአሜሪካ ፤ አውሮፓ እና በአፍሪካ በተለያዩ ሀገሮች በበርካታ ከተሞች ላይ እጅግ ብዙ ሺህ ህዝብ የሚገኝበትን የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ እንደተዘጋጁና የቤት ስራቸውን ቀድመው እንዳጠናቀቁ ለማወቅ ችለናል ፤ ይህ ጊዜያዊ ኮሚቴ ከዚህ በተጨማሪም አለማቀፋዊ ለሆኑ ተቋማት የኢትዮጵያ መንግስት የሚሰራውን ስራ በመቃወም ደብዳቤዎችን መላክ ችሏል ፤ ሀገር ቤት የሚገኝው ምዕመን ግን ከመንግስት ሊመጣ የሚችለውን ነገር በመፍራት እንደ ባለቤት ሲንቀሳቀስና ጥያቄውን ቢያንስ እንኳን ለቅዱስ ሲኖዶስ እና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲያቀርብ አልተመለከትንም ፤ ይህ በህዝቡ ውስጥ ያለውን ከልክ ያለፈ ፍርሀት እንደማሳያ ሆኖ ሊወሰድ ይችላል ፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ብዙ ሰዎች የማህበረ ቅዱሳንን ሪፖርት ሲጠባበቁ ነበር ፤ ማህበሩ የሚጠበቅበትን ስራ በማከናወን የአቅሙን ያህል ሪፖርት ማቅረብ ችሏል ፤ እንደ እኛ ሀሳብ ከአሁን በኋላ ያለው ስራ የእኛ የምዕመናን እንጂ የማንም አይደለም ፤ ሪፖርቱ ብቻውን መፍትሄ አይሆንም ፤ “ፈረስ ያደርሳል እንጂ…..” የሚባል ተረት አለ፡፡ እኛ ጉዳዩን ጉዳያችን በማድረግ ሁሉም ምዕመን በግልም ሆነ በህብረት  ስራ መስራት ካልቻለ ማንም መጥቶ ገዳሙን ከሸንኮራ ተክል ሊታደገው አይችልም ፤ ነገሮችን “እግዚአብሔር ያውቃል” ብለን ለአምላክ አሳልፈን መስጠት ያለብን መጀመሪያ የአቅማችንን ሙከራ አድርገን መሆን መቻል አለበት ፤   

3.    የፖለቲካ አይዲዎሎጂ፡- ይህ ፖለቲካ የሚባል ነገር በአሁኑ ሰዓት ነቀርሳ ያልሆነበት ሰውና ተቋም ለማገኝት ይቸግራል ፤ አንዱ ይህ ነገር ችግር ከሆነበት ቦታ ቤተክህነቱ ነው ፤ መንግስትን ለማስደሰት ሲሉ መደረግ የሌለበትን ነገር ሲያደርጉ መመልከት አዲስ ነገር አይደለም ፤ ፖለቲከኞቹ ስለሚሰራው የስኳር ልማት ገለጻ ሳያደርጉ ልወደድ ባዮችና ክሬዲት ማግኝት የሚፈልጉ አቶ ተስፋዬን የሚመስሉ ሰዎች የሚገኙበት ነው፡፡ እምነት ደግሞ የፖለቲካ ተቃራኒ ነው ፤ ምንም አንድ የሚያደርጋቸው ነጥብ የለም ስለዚህ ፖለቲከኛ ሆኖ የቤተክርስትያኒቱን ወንበር ሳይገባቸው የያዙ ሰዎች ባላቸው የገዥው ፓርቲ ደጋፊ አቋም መሰረት ለመቃወምም ሆነ ለመደገፍ አስቸጋሪ ሁኔታ እየፈጠሩ ይገኛሉ ፤ መንግስት የሚፈልገው የሱን ስራ እንዲደግፉለት ነው ፤ እነርሱም ለጊዜው አይናቸው ይታወርና በጭፍን መለስ ዜናዊ ስለተናገረ ብቻ ፤ አባይ ጸሀዬ ስላወሩ ብቻ በነርሱ ጎራ ሲቆሙ እየተመለከትን ነው፡፡ ‹‹ህዝቡ ስኳር እየተቸገረ ነው ›› ብለው ባለስልጣናቱ ተናግረው ሳይጨርሱ እነርሱ የገደል ማሚቱ ሆነው ድምጹን ሲያስተጋቡ እየተመለከትን ነው ፤ ፖለቲካ የዘመኑ የቤተክርስትያን ፈተና ሆኖም እየተመለከትን ነው፡፡

4.    የአባቶች በሁለት ጎራ መቆም ፡- ይህን ፕሮጀክት ላይ ጥርት ያለ አቋም ያላቸው አባቶች እንዳሉም ሌሎች አባቶች ደግሞ ፕሮጀክቱ ላይ ሀሳብ የማይሰጡም ይገኛሉ ፤ የትግራይ ክልል ሊቀ ጳጳስ ውዝግቡ ሲጀመር በጸሎት ከማስጀመር ያለፈ መናገር አለመፈለጋቸው እናውቃለን ፤ የጎንደር ሊቀ ጳጳስም መጀመሪያ ላይ የነበራቸውን አቋም እስከ መጨረሻ ማስኬድ አለመቻላቸውም የሚታወቅ ነው ፤ ታዲያ በተግባር እንዲህ ያደረጉት አባቶች ሁለት ቢሆኑ እንኳን ሌሎቹም እንዲህ አያደርጉም ማለት የሚከብድ ይመስለናል፡፡ አቡነ ጳውሎስ በዚህ ጉዳይ ላይ ደግፈው በእርሳቸው በኩል አቡነ ፋኑኤልን እና አቡነ ገሪማን የመሰሉ አባቶች እንደሚያሰልፉ እሙን ነው ፤ ሌሎች አባቶች ደግሞ አቋማቸው የእርሳቸው ተቃራኒ ሊሆን ይችላል ፤ ዝም ማለትም የሚፈልጉ አባቶች ሊፈጠሩ ይችላሉ ፤ በዚህ ጊዜ የሚፈጠረው አለመግባባት ሌላ ችግር እንዳይፈጥር በመስጋት ይህ ጉዳይ ላይ ከመንግስት መጥቶ እንወያይ እስኪላቸው ድረስ ማቆየቱን የወደዱ ይመስላሉ፡፡

5.    መንግስትን መጠበቅ ፡- ጉዳዩ ላይ ለጊዜው መንግስት ዝምታን ስለመረጠ አባቶችም ይህችን ክፍተት በመጠቀም መንግስት ጉዳዩን ሲያመጣው ብቻ መነጋር የፈለጉ ይመስላል ፤ መንግስት ስራውን ባላመነበትና ዘወትር በሚዋሽበት ሁኔታ ላይ አጀንዳ አድርጎ በጉዳዩ ላይ መነጋገር ከመንግስት ሌላ ጥያቄ እንዳያስነሳም ያሰጋል ፤ “ዋልድባ ገዳም ምን ሆነና ነው በዚህ ጉዳይ ለመነጋገር አጀንዳ የያዛችሁት?” ብሎ ቢጠይቅ ለጥያቄው መልስ መስጠት የሚችሉ የአባቶቻችን ብዛት ከጣቶቻችን አይበልጡም ፤ እንደ አቡነ ፋኑኤል ያሉት አባቶች አቋማቸው ቀድሞ ይታወቃል ፤ አቡነ ፋኑኤል በግልጽ ተናገሩ እንጂ ይህ ጉዳይ ተደርጎ በአጀንዳነት ቢያዝ ኖሮ አቡነ ጳውሎስ እና ሌሎች አባቶች እንደሚከተሏቸው ይታወቃል ፤ ድምጻቸው ሚዛን ባይደፋም ፤ ጉዳዩን ሳይነጋገሩበት በስተመጨረሻ ቀን ቃለጉባኤው ላይ ሊያስፈርሟቸው የነበረውን ሀሳብ ለተመለከተ ሰው ቢወያዩበት ኖሮ ምን ይፈጠራል ? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ አያስቸግረውም የሚል እምነት አለን፡፡

6.    ከመጠን ያለፈ ፍርሀት ፡- እውነቱን ለመናገር ከአቡነ ጳውሎስ ጀምሮ ሁሉም በሚያስብል መልኩ መንግስትን እና የመንግስትን ባለስልጣናት በሚሰሩት ተገቢ ያልሆነ ስራ ስለ እውነት ብለው የሚጋፈጡ አባቶች አሉ ለማለት አያስደፍርም ፤ ከ2 ወር በፊት ጎንደር ላይ ዋልድባን በማስመልከት ‹‹ምህላ አውጃለሁ›› ያሉ አባት ከመንግስት “ምን ተፈጠረ እና ነው ምህላ የሚያውጁት?”` የሚል ጥያቄ ሲመጣ ‹‹ምህላ ማወጅ መብቴ ነው ፤ የእናንተን መልስ መጠበቅ አይጠበቅብኝም›› ብለው የመለሱት ቆራጥ አባት በተደረገባቸው ተጽህኖ አማካኝነት ‹‹ ዋልድባ ላይ ውሀ ቢፈስ ምን ችግር አለው ፤ ገነትም እኮ ውሀ ይፈስባታል›› በማለት ከአቋማቻ ሸርተት ማለታቸው ይታወቃል፡፡  ይህ ማለት ስለ እውነት ብለው ለተናገሩት ነገርና መጀመሪያ የነበራቸውን አቋም እስከመጨረሻ ይዞ አለመዝለቅ ችግር እንዳለ ያሳየናል ፤ ይህ ደግሞ ፍርሀት ብቻ ነው ሊባል የሚችለው ፤ ከጎንደርና  አካባቢው ዓመታዊ የመድሀኒአለም በዓል ለማክበር እና ዋልድባ ገዳም ያለበትን ሁኔታ ለመመልከት በርካታ ወንድሞችና እህቶች ወደ ቦታው መሄዳቸው የሚታወቅ ነው ፤ ቦታው ድረስ ሂደው ተመልክተው የመጡትን ነገርና በመንግስት ወታደሮች ያለአግባብ የደረሰባቸውን ጉዳት ለአቡነ ኤልሳዕ ሊያስረዷቸው ወደ ሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት  በመሄድ መናገር ሲጀምሩ ከአቡነ ኤልሳዕ ያገኙት መልስ “ስለሚታረሰው አያገባችኹም፤ ስለተተኮሰባችኹና ስለተደበደባችኹት አያገባንም” የሚል  ነበር ፡፡ ለዚህ ከመጠን ያለፈ ፍርሀት እንደማሳያ ከዓመታት በፊት በተደረገው የዩንቨርሲቲ ተማሪዎች አመጽ ቤተክርስትያን የገቡትን ተማሪዎች ኦራል መጥቶ አፍሶ ሲወስዳቸው ሁለት አይነት አቋም መንጸባረቅ ችሎ ነበር ፤ የፈሩት ‹‹ይውሰዷቸው ›› ሲሉ ሌሎቹ ደግሞ ‹‹አይሆንም›› ያሉ እንደነበሩ በጊዜው መመልከት ተችሏል ፡፡ በጊዜው የደህንነት ኋላፊው አቶ ክንፈ መጥቶ ቤተክርስትያን የገቡትን ተማሪዎች በንቀት ተመልክቶ ካበቃ በኋላ ‹‹ስንቱ ታጋይ በርሀ ላይ ወድቋል እናተም ሰው ሆናችሁ ታምጻላችሁ? ለአንድ ተማሪ አንድ ጥይት ይበቃናል…››ብሎ በተናገረ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ጦር ኃይሎች መኮንንኖች አዳራሽ የድርጅት ስብሰባ አድርጎ ሲወጣ አንድ ጓደኛው በጭንቅላቱ 2 ጥይት እንደለቀቀበት የዓመታት ትውስታችን ነው፡፡ በቤታችን ውስጥ ለማድረግ የሚታሰብንና በተደረገ ነገር ላይ አቋም መያዝ አለመቻል ከፍርሀት ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? 

7.    መሰልቸት ፡- በአሁን ሰዓት የሚገኙ የሲኖዶስ አባላት እጅጉን በእድሜ የገፉ መሆናቸው ይታወቃል ፤ በቀን ለ8 ሰዓታት ያህል ለ16 ቀናት ሳይሰለቹ ስለ ህዝበ ክርስትያን እና ስለ ቤተክርስትያን አንድነት ሳይታክቱ ስብሰባ መቀመጥ ቀላል የሚባል ነገር አይደለም ፤ በዚህ ስብሰባ ላይ በህመም ምክንያት አንዳንድ አባቶች ቤት ማረፍ ቢገባቸው እንኳን “ቤተክርስትያንን ለአቡነ ጳውሎስ አሳልፌ አልሰጥ” በሚል ሀሳብ ከነህመማቸው ስብሰባው ተጀምሮ እስከሚያልቅ ድረስ የስብሰባው ሂደት ላይ የነበሩ አባቶች እንዳሉ ለማወቅ ችለናል ፤ ከአጀንዳዎቹ ብዛትና ከቀኑ ብዛት የተነሳ አባቶች ቢሰለቹም አይፈረድባቸውም ፤ በተቻላቸው መጠን ያህል አጀንዳዎቹን መመልከት እና ውሳኔ ማሳለፍ ችለዋል ፤ ተፈጻሚነቱ ላይ ጥያቄ ቢኖርም ፤ ከዚህ ረዥምና አሰልቺ የስብሰባ ጊዜያት በኋላ ይህን ጉዳይ ተነጋግረው አቋም ይወስዳሉ ማለት ይከብዳል፡፡

8.    የአቡነ ጳውሎስ ተጽህኖ ፡- አቡነ ጳውሎስ የሚያሳድሩት ተጽህኖ ቀላል የሚባል አይደለም ፤ የባለፈው ሲኖዶስ ስብሰባ ጊዜ ሲኖዶሱ ይፍረስ ብሎ የወሰነውን የአቡነ ጳውሎስን ጣኦት በተጽህኖ አማካኝነት እስከ አሁን ሳይፈርስ በቦታው ተቀምጦ አለ ፤ እርሳቸው ካመኑበት ሌሎች አባቶችን ከጎን ማሰለፉን ተክነውታል ፤ ይህ የዋልድባ ገዳም ጉዳይ ላይ የሳቸው አቋም ፕሮጀክቱ ቢሰራ ችግር የለውም የሚል ነው ፤ ይህ የታወቀው አባቶች ስብሰባን ጨርሰው ቃለጉባኤ ለመጻፍ የተወከሉ አባቶች ተጽፎ በጉባኤው ማጠናቀቂያ ላይ ሲነበብላቸው ‹‹በዋልድባ ገዳም ላይ የሚሰራውን የስኳር ልማት እንደግፋለን›› የሚል ሀሳብ ያለው ሲሆን ፤ ‹‹ይህን ጉዳይ ተነጋግረን አቋም ያልወሰድንበት ሳለ እንዴት እዚህ ውስጥ ሊጠቃለል ቻለ?›› የሚል ጥያቄ በመነሳቱ አባቶች  ከቃለ ጉባኤው ላይ ማሰረዝ ችለዋል፡፡ ይች አካሄድ በአንድም ሆነ በሌላ አቡነ ጳውሎስ የሚደግፏት ሀሳብ መሆኑ ግልጽ ነው ፡፡ ስለዚህ አቡነ ጳውሎስ ጉዳዩን ከአባቶች ጋር ባይነጋገሩበትም መስመራቸውን መመልከት ችለናል ፤ የያዙት መንገድ ያዝልቃቸው አያዝልቃቸው የምናውቀው ነገር ባይኖርም፡፡

ምንጭ: አንድ አድርገን ብሎግ

Read Full Post »

(ማኅበረ ቅዱሳን)፡-በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በየወሩ እየተዘጋጀ የሚቀርበው የዜና ገዳማት መርሐ ግብር ግንቦት 7 ቀንYemeba Serchet to Monks 2004 ዓ.ም. ተካሔደ፡፡ በዋነኛነት ከየካቲት 24 እስከ መጋቢት 4 ቀን 2004 ዓ.ም. ድረስ በቆየው የመብዐ ሳምንት በሚል በችግር ላይ ለሚገኙ 400 አድባራትና ገዳማትን ለመርዳት ከምእመናን የተሰበሰበን መብዐ እና አልባሳት /ልብሰ ተክህኖ/ ስርጭት ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ 800 ሺህ ብር ለመሰብሰብ የተቻለ ሲሆን እስከ 750 ምእመናን ተሳትፎ አድርገዋል በማለት የገለጹት የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ናቸው፡፡ በተገኘው ገቢ መሠረት ስርጭቱን በ4 ዙር ለማከናወን የታቀደ ሲሆን በመጀመሪያው ዙር በትግራይ 7 ሀገረ ስብከቶች ውስጥ ለሚገኙ 50 አድባራትና ገዳማት እንዲሁም አብያተ ክርስቲያናት ለአንድ ዓመት የሚሆን የመብዐ ስጦታ ተሰጥቷል፡፡

ስጦታው የተከፋፈለው ለአንድ ሳምንት የቆየ ጉዞ በማከናወን በየአድባራቱና ገዳማቱ በመገኘት ሲሆን ስርጭቱ ካካተታቸው ሀገረ ስብከቶች መካከል በደቡብ ትግራይ አርማጭሆ፤ እንደርታ፤ አዲግራት፣ አክሱም፣ ሽሬና ሁመራ ይገኙበታል፡፡ ከገዳማቱ መካከል ደብረ ሳሙኤል ዘሃሌ ሉያ፣ ደብረ በንኮል አቡነ መድኀኒነ እግዚእ፤ አባ ዮሃኒ ዘቆላ ተንቤን፣ አባ ቶማስ ዘደብረ ማርያም ዘሃይዳ፣ ፀአዳ አምባ አቡነ መርአዊ ክርስቶስ፣ እንደቆርቆር ቅድስት ማርያም ገዳማት ይገኙበታል፡፡
አድባራቱና ገዳማቱ ሰው የማይደርስባቸው ሊባሉ የሚችሉ በረሃማና ጠረፋማ አካባቢዎች ሲሆኑ እቅዱን ለማሳካት አስፋልቱንና ኮረኮንቹንYeMeba Serechetበመኪና፤ ተራራውንና ተዳፋቱን በግመል በመጫንና በማከፋፈል ምንም መቀደሻ እጣን፣ ጧፍ፣ ዘቢብ እንዲሁም ልብሰ ተክህኖ ለሌላቸው ለማዳረስ ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡ ስርጭቱን የተቀላጠፈ ለማድረግ በየሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የማኅበሩ ማእከላት አባላት ድርሻ ከፍተኛ ነበር፡፡
በስጦታው ወቅት አባቶች ያሉባቸውን የመብዐ እጥረት ገልጸው “ዛሬ ዐይናችን እንደበራ እንቆጥረዋለን” በማለት የተደረገላቸውን ስጦታ ውዳሴ ማርያም እየደገሙና የኪዳን ጸሎት እያደረሱ መብዐውን ለሰጡ ምእመናንና ማኅበረ ቅዱሳን በጸሎት በማሰብ ተቀብለዋል፡፡
በተያያዘም በዋነኛነት ትኩረት ከተደረገባቸው ገዳማት ውስጥ ትግራይ ፀአዳ አምባ አቡነ መርአዊ ክርስቶስ ገዳም ይገኝበታል፡፡ ታላላቅ አባቶችን ያፈራ ገዳም እንደሆነና በረሃብና እርዛት፤ እንዲሁም ሆድ በሚነፋ በሽታ ምክንያት አባቶች በችግር ላይ እንደሚገኙ የተገለጸ ሲሆን እውነታውን በፊልም በማስደገፍ ለምእመናን ቀርቧል፡፡ በሽታው በጥናት ሊደረስበት እንዳልተቻለ መነኮሳቱ የሚገልፁ ሲሆን የአካባቢው ምእመናን በበሽታው ምክንያት ወደ ሰፈራ በመሄዳቸው ገዳማውያኑ ብቻቸውን ቀርተዋል፡፡ ከገዳሙ የሁለት ሰዓት የእግር ጉዞ በኋላ የእርሻ ቦታ ያላቸው ቢሆንም የገዳሙ አባቶች በእርጅናና በጤና መታወክ ሳቢያ ማረስ አልቻሉም፡፡ ከዚህ ቀደም የአካባቢው ምእመናን ያርሱላቸው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ “አበው ያቆዩልንን ቅርስና ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ጥለን አንሄድም” በማለት ጸንተው ቆይተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት 52 መነኮሳት ብቻ የሚገኙ ሲሆን በአልባሳትና በምግብ እጥረት እየተሰቃዩ ይገኛሉ፡፡ በዚህም ምክንያት የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ትኩረት አድርጎ ለእነዚህ አባቶች ምእመናን እንዲደርሱላቸው ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡ እስከ ነሐሴ 2004 ዓ.ም. ድረስ ለአልባሳት 15.600 ብር እንዲሁም ለቀለብ 20.800 ብር እንደሚያስፈልግ በመርሐ ግብሩ ወቅት በመገለጹ በእለቱ ከተገኙ 2 በጎ አድራጊ ምእመናን ከላይ የተጠቀሱትን ወጪዎች እንደሚሸፍኑ ቃል ገብተዋል፡፡ ዋና ክፍሉም ምስጋናውን በማቅረብ ምእመናን ድጋፋቸውን እንዳይለይ አጽንኦት በመስጠት “እናንተ ሁል ጊዜ ስጡ፣ ከቅዱሳን በረከትን ታገኛላችሁ፣ እጃችሁ ከምጽዋት አይጠር፣ እኛም አደራችሁን ተቀብለን አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ ነን” በማለት የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ገልጸዋል፡፡
በዜና ገዳማት ወርሐዊ መርሐ ግብር ከተዳሰሱት መካከል ለዝቋላ ገዳም በቃጠሎው ምክንያት ጊዜያዊ ድጋፍና የፕሮጀክት ጥናት መደረጉ ተገልጿል፡፡ በቃጠሎው ወቅት የቀለብ እጥረት በመከሰቱ ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናንን በማስተባበር 50 ኩንታል ስንዴ፣ 20 ኩንታል ጤፍ፣ 40 ሺህ ብር የሚገመት ውኃ፣ በሶ፣ ስኳርና ዳቦ ድጋፍ ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላትና ከበጎ አድራጊ ምእመናን የተሰበሰበ ለድጋፍ የሚሆን 125 ሺህ ብር ተሰብስቧል፡፡ ወደ ዝቋላ ገዳም ባለሙያዎችን በመላክ ለገዳሙ የሚሆን የእርሻ ቦታ፣ የመጠጥ ውኃና የመንገድ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችል ጥናት ተደርጓል፡፡ የደብረ ዘይት ማእከል አባላት የዝቋላን ገዳም አስቸጋሪ መንገድ ለመጠገንና ለማስተካከል ምእመናንን በማስተባበር ከፍተኛ ርብርብ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ የጎንደር ወደብረ ጥበባት በዓታ ለማርያም ገዳም የአብነት ተማሪዎች ማደሪያ ቤት ግንባታ መጀመሩም በሪፖርቱ ከተካተቱት አበይት ክንውኖች አንዱ ሆኗል፡፡
በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር በዲ/ን አእምሮ ይሄይስ በክፍሉ የተከናወኑ ፕሮጀክቶችን አስመልክቶ የ10 ዓመት ሪፖርት አቅርበዋል፡፡ በሪፖታቸውም በእርሻ ፤ንብ ማነብ፤ግንባታ፤ የወተት ላምና ከብት ማድለብ እንዲሁም ሰው ኃይል ማፍራት ላይ ያተኮሩ ፕሮጀክቶች ተሠርተዋል፡፡ ከፕሮጀክቶቹ መካከል በአብዛኛው የአብነት ትምህርት ቤት ግንባታ፣ የመምህራንና የተማሪዎች መኖሪያ፤ የጉባኤ ቤትና የካህናት ማሠልጠኛ፣ የካህናትና መነኮሳት መኖሪያ ግንባታ ፕሮጀክቶች ሰፊውን ድርሻ እንደሚይዙ በስፋት አብራርተዋል፡፡ በጥናት ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በሂደት ላይ ሲሆኑ ከእቅድ ውጪም እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች ይገኛሉ፡፡በተጨማሪም 145 የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ 136 መምህራን፤ 865 ተማሪዎች በየወሩ እየተደጎሙ እንደሚገኙ ዲ/ን አእምሮ ይሔይስ ገልጸዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ ላይ በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲሆን የ3 ወራት የሒሳብ ሪፓርት ቀርቧል፡፡ ከምእመናን በክፍሉ እንቅስቃሴና በገዳማት ዙሪያ አስተያየት ተሰጥቷል፡፡ ከ800 በላይ ጥሪ የተደረገላቸው በመብዐ ሳምንት ድጋፍ ያደረጉ ምእመናንና በጎ አድራጊዎች በመርሐ ግብሩ ላይ ተሳትፈዋል፡፡
ዜና ገዳማት በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በየወሩ እየተዘጋጀ የገዳማትንና አድባራትን ነባራዊ ሁኔታ፣ የክፍሉን እቅዶችና ተግባሮች እንዲሁም የተተገበሩና በዝግጅት ላይ ያሉ ፕሮጀክቶች የሚተዋወቁበት መርሐ ግብር መሆኑ ይታወቃል፡፡
ምንጭ: አሐቲ ተዋሕዶ 

Read Full Post »

ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም፤

ዛሬም ጉድ ተሰማ ከዋልድባ ገዳም፤

ካባቶቼ ሃገር አበረንታንት ገዳም ።

ዛሬም ጉድ ተሰማ ከሰሜን ተራራ፤

ወልቃይት ጠገዴ ከቅዱሳን ጎራ፤

ጸለምት ማይ ፀብሪ በተራ በተራ።

በጌታ ቡራኬ በቅዱሳን ጸሎት፤

በርስት ያገኘነው ካበው ከቀደሙት፤

ላይጠፋ ዘላለም የገደሙት ገዳም፤

የህይወት ምንጭ ሆኖ የቆየው ለዓለም፤

ምን ተገኘ ዛሬ ከዋልድባ ገዳም፤

ማረስ ያስፈለገ መንገዱን ማጣመም።

የገዳማት በኩር የቅዱሳን ዋሻ፤

ምንድነው ዝምታህ ስትታጭ ለርሻ።

አንተ ቅዱስ ስፍራ ጌታ የመረጠህ፤

ከምድራዊው ገነት ተራራው ስር ያለህ።

እህል አይግባብህ ሃጢያት አይሻገር፤

ብሎ ሲገዝትህ አምላክህ ሲናገር።

አልሰማህውም ወይ ዝምታህ በረታ፤

ሰንጥቀው ሲወስዱ ካለህበት ቦታ።

አይደል ለኢትዮጵያ ለመላው ዓለም፤

ጸሎትህ የበጀው ዋልድባ ገዳም።

እልፍ መነኮሳትን ጠልለህ ያስቀመጥክ፤

ህዝቡን እያማለድክ ለጌታ ያቀረብክ ።

ምነው ዝም አልክ ዛሬ ለሸንኮራ ሲያጩህ፤

በዋጋ ሊሸጡ ፊትህ ሲስማሙብህ።

ከማር የሚጣፍጥ ቃል አለቀብህ ወይ፤

ሊቃውንት ሰባኪ ልጅስ የለህም ወይ፤

ሸንኮራ ሊያበቅሉ የመጡብህ ከላይ።

ውለታህን ቆጥሮ አንትን የሚታደግ፤

ታሪክ አመስጥሮ ስላንተ የሚነድ፤

እንደሻማ ቀልጦ ብርሃኑን የሚሰጥ፤

ጠላት አሳፍሮ ምርኮ ሚገለብጥ።

አሳየኝ ልጅህን ዋልድባ ንገረኝ፤

አበረንታንት ጀምር ተስፋ አታስቆርጠኝ።

የቀደመው ታሪክ ሁሉም ተዘንግቶ፤

እልፍ መነኮሳት ያኖረው አስማማምቶ፤

ያ የገነንክበት ታሪክ ዳብዛው ጠፍቶ፤

ለሸንኮራ ሲያጩህ ልጅህ አንገት ደፍቶ።

ዝምታን መረጠ በአርምሞ ከተተ፤

እስኪመስል ድረስ ባንት የተገዘተ።

ዝቋላ ሲያለቅስ ሲውል እርቃኑን፤

አሰቦት ሲቃጠል ሊያስተዛዝን አንተን።

ማቃቸውን ለብሰው ሙሾ ሲወርዱልህ፤

የገዳማት በኩር ብለው ሲያዜሙልህ።

ልጅህ ግን ዝም አለ በአርምሞ ከተተ፤

እስኪመስል ድረስ ጥንት የተገዘተ።

የጣና ገዳማት ዝምታን መረጡ፤

አክሱም ጽዮን ማርያም ሃዘንም አልወጡ።

ታች ደብረሊባኖስ በዝምታ አለፈው፤

ቅዱስ ላሊበላም ነገሩን ረሳው።

አሁን ማነው ላንተ ዋስና ጠበቃህ፤

ንገረኝ ልንገረው እንዲሟገትልህ።

ሸንኮራ ሳይዘሩት አጽሙን ሳያፈልሱት፤

ዳብዛህን ሰውረው ወዝህን ሳያጠፉት፤

ደርሶ ቢታደግህ ከዚህ ሁሉ ጥፋት።

ንገረኝ ልንገረው እንዲሟገትልህ፤

ተጠብቆ እንዲኖር ርስትና ጉልትህ።

አንተዝም ብትል አርምሞን ብትመርጥም፤

ስላንተ ተሟጋች ቃል ባትናገርም።

እስካለሁበት ቀን ካልሞትኩ በስተቀር፤

አላይም ሲያፈርሱህ ሲያመርቱብህ ስኩዋር።

ድንበርህን አፍርሰው ወንዝህን ተሻግረው፤

መካናቱ ወድቀው ከማያቸው ፈርሰው።

አሁን እሄዳለሁ ስላንተ እዘምታለሁ፤

ቃልኪዳን ገባሁኝ እስከመጨረሻው እሰዋልሃለሁ።

እናንት ገበሬዎች ስኩዋሩን አልሚዎች፤

የኢትዮጵያ ገዢ አስተዳዳሪዎች።

ዛሬ ምን አያችሁ ከዋልድባ ገዳም፤

ካባቶቼ ርስት አበረንታንት ገዳም።

መሬቱን ልታርሱ ድንበር ልታፈርሱ፤

ቅርስ መዝብራችሁ ሰው ልታስለቅሱ።

ለምን ደፈራችሁ ነገሩኝ ሚስጥሩን፤

ልቤም አይሸበር ልረዳ ነገሩን።

ታሪክ አታውቁም ወይ ነጋሪስ የለም ወይ፤

ከእግዜር ጋር መጣላት አያሳፍርም ወይ።

የቀደሙት ሁሉ ከመንገድ የወጡት፤

ከወንበራቸው ላይ የተገለበጡት፤

ከክብር ወደታች በግፍ የወረዱት።

የእግዚአብሄርን መንበር ሲገዳደሩት ነው፤

ቅዱሳን አበውን ሲያስጨንቁዋቸው ነው።

አሁንም ልምከርህ አንድም ብለህ ጀምር፤

ከቀደመው ታሪክ ጥቂት እናመስጥር።

ሰው ከሰው ጋር ታግሎ ሰውን ያሸንፋል፤

በጉልበት ሃያላን ድል ሲመቱ አይተናል፤

ዳዊት ጎልያድን በጠጠር ጥሎታል፤

በአህያ መንጋጋ ሽውን አርግፎታል።

ነገር ግን ከጌታ ከእግዚአብሄር ተጣልቶ፤

ድል የቀናው የለም ያሸነፈም ከቶ።

ማሰብም ድፍረት ነው አይደለም መታገል፤

አሁን ልብ ግዛ በጣምም ቸል አትበል።

ዋልድባን ለማየት ብሩህ አይን ከለህ፤

ውሳጣዊ አይንህን ጌታ ካበራልህ።

ሂድ ግባ ሱባኤ ትጋበት ለፀሎት፤

ሸንኮራው ይቅርብህ አለ የሚበሉት፤

አንተም ትበላለህ ከፈለግክ ድህነት።

አልቀበልም ካልክ ልብህ ከታወረ፤

ለጥፋት ዘመቻ አንገትህ ከዞረ።

አወዳደቅህን ከአሁኑ አሳምረህ፤

መንገድህን ጀምር ሂድ ብያለሁ ይቅናህ።

በታሪክ ማህደር በዚያ ክብር መዝገብ፤

በግራ ተጽፎ ለህዝቡ ሲነበብ።

የተጓዝከው ጉዞ ያደረግከው ድርጊት፤

የሰራሀው ወንጃል ያጠፋሀው ጥፋት፤

ከመሃመድ ጋራ የተባበርክበት።

ለጥፋት ዘመቻ የተዛመድክበት፤

ዮዲትንም በግብር የተመሰልክበት፤

ተጽፎ ይቀራል በታሪክ መዛግብት።

ማጥፋትህም ሁሉ ለህዝብ ይነገራል፤

አንትም ትሄዳለህ ዘመንህ ያበቃል፤

ዋልድባ አበረንታንት ዘላለም ይነግሳል፤

እስከመጨረሻው ሲዘከር ይኖራል፤

ላይጠፋ ዘላለም በአለት ላይ ታንጿል፤

ጽኑ ቃል ኪዳኑ በክብር ተጽፏል።

ፍኖተጽድቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፈለገ ሃዋርያት ሰንበት ትምህርት ቤት

መጋቢት ፳፻፬ ዓ.ም.

ማናየ አለማየሁ።

ሙሉውን ግጥም ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

Read Full Post »

ተነስ!
ተነስ ከተኛህበት ንቃ
እምነታችን እንድትኖር ተጠብቃ
ያንቀላፋህ ቶሎ ንቃ
እምነትህ ላይ ፈተናዎች ተደቅነው
አህዛቡ ገዳማቱን ሲያቃጥለው
ዋልድባንም መንግስታችን ገብቶ ሲያርሰው
እስከመቼ ነው ዝም የምንለው?
በቃ! እንበል ዋልድባችን አይታረስ
ገዳማችንንም አታፍርስ!
ተነሳሁኝ አንተም ተነስ
እንባባል በአንድ መንፈስ።
ከአብነት ለወየሁ (ግንቦት 2004 ዓ.ም)

ለምን ይሆን ዝምታሁ?

ጥቁሩን ቆብ የደፋችሁ
የመከራውን መገለጫ ጥቁር ቀሚስ ለብሳችሁ
የማይገኘውን ክብር አግኝታችሁ
በመድረክ ላይ ሰብካችሁ
የጌታን ፍቅር መስክራችሁ
የሰማዕታትን ታሪክ ተናግራችሁ
ሰማዕት ሁኑ እያላችሁ
እንናንተ እንዳትሆኑ ምን ያዛችሁ?
ስታስተምሩ ስንሰማችሁ
መነኮሰ ሞተ ካላችሁ
እኮ የታል መሞታችሁ?
ወይስ እንደ ባሕርዛፍ መልሳችሁ አበባችሁ
የዚህች አለም ውጥንቅጧ እንቅ አድርጎ ያዛችሁ
አሁን ይብቃ አይታሰር ምላሳችሁ
ለስጋዊው ሞት አትፍሩ እንዳላችሁ
እኛም አትፍሩ ብለናል ልጆቻችሁ
በሉ እዘዙን እንስማችሁ
የገደማችሁባት ገዳም ተምር ያያችሁባት ቦታ
እንዴት በእናንተ ዝምታ ገዳማችን ይፈታ
በሉ እንጂ ተናገሩ ዝምታውን ስበሩት
አርምሞአችሁን አይተው ገዳማችንን ደፈሩት
በታሪክ ተወቃሽ ናችሁ በእኛ ዘመን ያላችሁ
ጥቁሩን ቀሚስ ለብሳችሁ ቃል ያልተናገራችሁ
መቼም ከእናንተ ነውና ቃሉን ከልቤ የሰማሁት
ያዕቆብ የኤሳውን ድርሻ ወስዶ በረከት እንዳገኘበት
እናንተም አፍ ላለው ሽጡት እምነቱን ይናገርበት።
ከአብነት ለወየሁ (ግንቦት 2004 ዓ.ም)

የግጥሙን ሙሉውን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

Read Full Post »

የታላቁ ገዳማችን ዋልድባን በኢትዮጵያ መንግሥት መደፈር ያስቆጣቸው ክርስቲያኖች በተለያዩ የአሜሪካን ግዛቶች ውይይት እያደረጉ እንደሆነ ከተለያዩ ከተሞች የደረሰን ሪፓርት ይገልጻል። በሳንዲያጎ ካሊሮርኒያ፣ በሚኒያ ፖሊስ ሚኖሶታ፣ በሻርለት ኖርዝ ካሮላይና፣ በቶሮንቶ ካናዳ ታላላቅ ሕዝባዊ ውይይቶች ተደረገው እንደነበረ መረጃዎች ደርሰውናል። በነዚህ በተለያዩ ከተሞች የተነሱት ውይይቶች ላይ እንደተረዳነው
፩ኛ/ አጠቃላይ ስለ ዋልድባ ገዳም ጂኦግራፊካል ገለጻ
፪ኛ/ ስለ ገዳሙ ወቅታዊ ሁኔታ ገለጻዎች
፫ኛ/ መንግሥት በሰጣቸው መግለጫዎች ላይ በመነሳት የባለሙያዎች ገለጻ
፬ኛ/ ክርስቲያኖች ምን ማድረግ እንደሚጠበቅብን እና
፭ኛ/ በመጪው June 4, 2012 ወይም ግንቦት ፳፯ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም. ስለተጠራው ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ

የተለያዩ አስተያየቶች፣ መግለጫዎች እና በቀጣይነት ምን መሠራት እንዳለበት ከስብሰባው ተሰብሳቢዎች እና ከውይይት አስተባባሪ ኮሚቴዎች መሰጠቱን ለመረዳት ችለናል።
በቀጣይነት እስከ June 4, 2012 ድረስ በተለያዩ ከተሞች ተመሳሳይ ስብሰባዎች እና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስብሰባዎች፣ የስልክ ኖንፈረንሶች በተለያዩ ከተሞች እንደሚደረጉ ለመገንዘብ ችለናል፥ በዚህም መሰረት በመጪው ጥቂት ቀናት ውስጥ

በዋሽንግተን ዲሲ የስልክ ኖንፈረንስ
በሚኒያፖሊስ ሜኖሶታ የውይይት መድረክ
በአትላንታ የውይይት መድረክ በዘጋጀቱን ለመረዳት ችለናል፥ ሙሉ መረጃዎቹ እንደደረሱን ለአንባቢያን እንገልጻለን።
እስከዚያው
ቸር ይግጠመን

Read Full Post »

  •    ሪፖርቱ የጠ/ቤተ ክህነት ሓላፊዎች “አቀረብን” ካሉት በይዘትም በተአማኒነትም የተሻለ ነው።
(ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 10/2004 ዓ.ም፤ May 18/ 2012/ READ THIS ARTICLE IN PDF)፦ ማ/ቅዱሳን መንግሥት በዋልድባ አካባቢው ሊሠራው ስላቀደው ግዙፍ ሮጄክት “አጠናሁት” ያለውን ሪፖርት አቀረበ፤ ከመንግሥት ጋር መነጋገሩንም ገለጸ። ዛሬ ይፋ የተደገው የማኅበሩ ሪፖርት የቤተ ክህነቱ አዳዲስ ተሿሚዎች ማኅበሩን በዋልድባ ጉዳይ በከሰሱ ማግስት የቀረበ ሲሆን ለእነርሱ ክስ የተሰጠ አፋጣኝ ምላሽ ይሁን አይሁን ወደፊት የሚታይ ይሆናል።

አዲስ የተሾሙት የሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ኃላፊ መምህር ዕንቁ ባሕርይ ተከስተ “በዋልድባ አካባቢ መንግሥት ሊሠራ ያቀደውን ግዙፍ የስኳር ፋብሪካን በማስመልከት በዋልድባ ይዞታ ላይ ያደረሰው ተጽእኖ መኖር አለመኖሩን የሚያጣራ ኮሚቴ ተቋቁሞ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሁሉ ተፈላጊውን የማጣራት ሥራ አከናውኖ” ከተመለሰ በኋላ “ጋዜጣዊ መግለጫ መሰጠቱና … የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች መከታተላቸው መሣተፋቸውና የሚፈልጉትን ጥያቄ በይፋ አቅርበው ምላሽ መሰጠቱ”ን ጠቅሰው “ማንኛውም ጋዜጠኛ በተለይም ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሣን የሆነው የማኅበሩ ጋዜጣና መጽሔት መረጃ ከወሰደ በኋላ መግለጫውን አለማውጣቱ አግባብነት የሌለው ከመሆኑም በላይ የሚዲያ ሥነ ምግባርንም ያልተከተለ ስለሆነ” ጽሑፉ ያልወጣበትን ምክንያት ማኅበሩ በጽሑፍ ይገልጽ ዘንድ ከሕዝብ ግንኙነት መምሪያ መታዘዛቸውን እንዳብራሩ መዘገባችን ይታወሳል።
የመምሪያው ደብዳቤ “ጋዜጣዊ መግለጫውን በሚዲያ ለማውጣት ተስማምታችሁ ሪፖርት እንድታደርጉ ከወሰናችሁ በኋላ ዘገባው የቀረበት ምክንያት በጽሑፍ ለማደራጃ መምሪያው” እንዲመለስ እንደሚጠብቅ በመግለጽ “ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ለብሔራዊ ደኅንነት አገልግሎትና ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን” ግልባጭ ተደርጓል። ደጀ ሰላምም “የቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ እና ሕግ አገልግሎት መምሪያ የቤተ ክርስቲያናችን አካላት ስለሆነ በቀጥታም ባይሆን ጉዳዩ ሊያገባቸው ይችላል። ከላይ ስማቸው የተዘረዘሩት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በምን አግባብ ነው ስለ አንድ ማኅበር፣ ያውም በአንድ መምሪያ ሥር ስላለ አካል ግልባጭ የሚደረግላቸው? መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶቹ ከሚዲያ ጋር የተገናኙ እንኳን ቢሆኑ በግድምድሞሽ “ግንኙነት አላቸው” ይባል ይሆናል። ፌዴራል ጉዳዮች፣ ደኅንነት፣ ፖሊስ … መጠቀሳቸው ለምን ያስፈልጋል? እሰሩልን፣ ግደሉልን፣ ቀፍዱድልን ለማለት ካልሆነ” ማለቷ ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ማኅበሩ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረውን የዋልድባ አጥኚ ቡድን ሪፖርት እጥር ምጥን አድርጎ አቅርቧል። ከመንግሥት ከቤተ ክህነትም መልስ ለሚፈልጉ ሰዎች የየድርሻቸውን በመስጠት ከነገሩ ጦም እደሩ ለማለት ሞክሯል። ከሀ-ሠ በተዘረዘሩ ዐበይት ዐዕማድ ርዕሶች የተዘረዘረው ሪፖርቱ ከአጠቃላይ ዳራ (Background) በመጀመር በማጠቃለያ ይፈጽማል። እነዚህም ሀ “ዳራ”፣ ለ “ዋልድባ ገዳምና አካባቢ ከመንፈሳውያት ተቋማት አንጻር” ፣ ሐ “በቅዱሱ ቦታ ድንበርና አካባቢ ስለሚገነባው ፕሮጄክት አጠቃላይ ዳሰሳ”፣ መ “ፕሮጄክቱ ላይ ገዳማውያኑ ያነሡአቸው ጥያቄዎችና የልዑካኑ ዕይታ”፣ ሠ “ማጠቃለያ” ናቸው።
ማኅበሩ በመንደርደሪያው ጉዳዩ ብዙ ወገኖችን ያነጋገረ፣ ያከራከረ መሆኑን ጠቅሶ “የጉዳዩን ምንጭ እና መፍትሔ ነጣጥሎ ማየት እስከሚከብድ ድረስ በሰው ልቡና ሲመላለስ ቆይቷል” ይላል። ምንጩን እና መፍትሔውን ለምን ለያይቶ ማየት እንደሚያስፈልግ አላብራራም። መፍትሔው የሚመጣው ለችግሩ ምላሽ ለመስጠት ከሚደረግ ጥረት መሆኑን (የcause and effect ግንኙነት) የዘነጋው ይመስላል።
ቀጥሎም “ከመጋቢት 25-30 ቀን 2004 ዓ.ም አምስት አባላት ያሉት የልዑካን ቡድን ወደቦታው” ተልኮ እንደነበር፤ “በቦታው በመገኘት ሁሉንም አካላት ማለትም የገዳሙን አባቶች፣ የፕሮጄክቱን ሓላፊዎች፣ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በማነጋገር ያገኘውን ምላሽ ከልዑካኑ ዕይታ ጋር በመጨመር ሰፋ ያለ ሪፖርት ይዞ” መመለሱን ጠቅሶ የማኅበሩ አመራር አካልም ሪፖርቱን “ከሰማ በኋላ፣ ከልዩ ልዩ አቅጣጫዎችና ተጨማሪ መረጃዎች ጋር በመመርመር” እንዳጸደቀው ይተርካል።
የማኅበሩ አመራር የቀረበለትን መረጃ “ከልዩ ልዩ አቅጣጫዎች” ማየቱ መልካም ቢሆንም  ከጠ/ሚኒስትሩ ንግግር እስከ መምህር ዕንቁ ባሕርይ ደብዳቤ ድረስ ማኅበሩ ከባድ ጫና ውስጥ መግባቱን ለሚያውቅ ማንኛውም ወገን ማለትም በመንግሥት ዘንድ “ሞገስ ያገኙት” ተሐድሶዎች እና ብሎጎቻቸው በተደጋጋሚ ሲሉት እንደነበረው መንግሥት በዋልድባ ዙሪያ የሚያካሒደውን “ፕሮጄክት” ለመቃወም በመላው ዓለም የተነሣው እንቅስቃሴ መሪ “ማኅበረ ቅዱሳን እንደሆነ” ተደርጎ መዘገቡ፣ ከአቦይ ስብሐት ጀምሮ ሌሎች የመንግሥት ባለ ሥልጣናት ጣታቸውን በማኅበሩ ላይ መቀሰራቸውን ለሚገነዘብ ሁሉ ሪፖርቱ በነጻነት የተዘጋጀ ነው ለማለት ይከብዳል። ለዚህም ፍንጭ የሚሰጠው በማጠቃለያው ላይ “ማኅበሩ በወልቃይት እየተገነባ በሚገኘው የስኳር ፕሮጄክትና በግድቡ ዙሪያ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ አጥንቶ ያዘጋጀውን ሪፖርት ከሚመለከተው ከፍተኛ የመንግሥት አካል ጋር ውይይት አድርጎ ነበር” የሚለው ዐቢይ ዐረፍተ ነገር ነው።
ጥናቱ በገዳሙ እና በመንግሥት መካከል ያለውን አለመግባባት ተመርኩዞ የተደረገ እስከሆነ ድረስ፣ ማኅበሩም በገለልተኝነት እና በሃይማኖታዊ ተቆርቋሪነት ነጻ እና ሙያዊ ትንተና ለመስጠት የፈለገ ከመሆኑ አንጻር ሪፖርቱን ሚዛናዊና ነጻ በሆነ መልክ ይፋ ከማድረጉ በፊት ለአለመግባባቱ አንድ አካል ማለትም ለመንግሥት “ከፍተኛ አካል” ቀድሞ ካቀረበ ምኑን “ነጻ ሪፖርት” ሆነው? “ከፍተኛ አካል” የሚለው በራሱ ከፍተኛነቱ ከትከሻ እስከ ራስ ድረስ ምን ያህል ከፍ እንዳለ ግልጽ ባይሆንም ሪፖርት አቅራቢው ክፍል ይህንን ሁሉ “ከፍተኛነት” ተቋቁሞ ለማለፍ አቅሙ እስከምን እንደሆነ ለማወቅ ይቸግራል።
የከፍተኛ ባለሥልጣኖችን አስፈሪ ግርማ ተቋቁሞ እውነቱን ብቻ በመናገር በኩል የቤተ ክርስቲያናችን መሪዎች ተፈትነው እንደወደቁ እናውቃለን። ከፓትርያርኩ እስከ ሌሎች አባቶች ድረስ ባለሥልጣናቱን ከመላእክት ባልተናነሰ እንደሚያከብሯቸው እና እንደሚፈሯቸው እናውቃለን። የማኅበረ ቅዱሳን ሪፖርት አቅራቢዎችና አመራር አካላት ይህንን የባለሥልጣናት “ግርማ” እና ውስጠ-ዘ መመሪያ ተቋቁመው “ነጻ ሪፖርት” ለማቅረብ ችለው ይሆን? ሪፖርቱ “ሐሰት” እንደሌለበት ብናምንም “ከእውነታው ላለመቆንጸሉ” ግን እርግጠኞች አይደለንም። ስለዚህም ይህ ሪፖርት ምን አዲስ ነገር ነገረን ብለን ለመጠየቅ እንገደዳለን። “አዲስ ነገር” ካልነገረን ደግሞ የቀረ ነገር መኖሩን እንጠረጥራለን። ያ የቀረው ነገር ምንድነው? ይዋል ይደር እንጂ መውጣቱ አይቀርም።
በጎ ጎኑን ከተመለከትን ሪፖርቱ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሓላፊዎች “አቀረብን” ካሉት በይዘትም በተአማኒነትም የተሻለ ነው። ለውይይት ጥሩ መነሻ  ይሆናል። መንግሥት ያዘጋጀውን ጥናት በአጭሩ ማቅረቡም ጥሩ ነው። የገዳሙን ታሪክ እና ማን ምን እንደሆነ ማብራራቱም በዋልድባ ጉዳይ የሚኖረን ውይይታችን መሠረት ያለው እንዲሆን ይረዳል። ፎቶዎቹ፣ ካርታዎቹ እና ዳሰሳዎቹ ጥሩ “ዳራ” ይሰጣሉ። ከዚህ የሚቀረው ፈረንጆቹ (reading between the lines) እንደሚሉት ከተጻፈው የማኅበሩ ሪፖርት ላይ በመመርኮዝ ያልተጻፈውን፣ አጠይሞ ያለፈውን እና ሳይናገረው በጥቅሻ ብቻ ያለፈውን ማብራራት ነው። እንዳለመታደል ሆኖ “ነጻ አስተያየት” የሚሰጡ አካላት የሚደቆሱበት አገር ስለሆነ ከማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በላይ መጠበቅ “ግፍ” ሊሆን ይችላል። ጭራሹኑ “እሳት ውስጥ” ግቡልን እኛ ዳር ቆመን እናያለን ከማለት እንዳይቆጠርብን፣ ያንንም ለማለት “ሞራላዊ ብቃታችን” ጥያቄ ውስጥ ስለሚገባ በሪፖርቱ ባንረካም “መቸስ ምን ይደረግ፣ አገሩ ኢትዮጵያ ሆነ” ከማለት ውጪ።
በጠቅላላው ሪፖርቱ አዲስ የውይይት በር ከመክፈት በስተቀር የተከፈተውን የተቃውሞ እና የውይይት በር የሚዘጋ እና እልባት የሚሰጥ ሊሆን አይችልም። ተቃውሞውም ይቀጥላል፤ ውይይቱም ይቀጥላል። አጭሩ መፍትሔ መንግሥት የጀመረውን ነገር ማቆም ብቻ ነው። ይዋል ይደር እንጂ መቆሙ ግን አይቀርም። ያለ ሕዝብ ተቀባይነት የሚጀመር ነገር መረሻው ምን እንሆነ በታሪክ እናውቃለን፤ በአገራችንም አይተነዋል። ደርግ መንደር ምሥረታ አለ፣ ልማት አለ፣ ገበሬውን ሰበሰበ … ለውድቀቱ ምክንያት ሆነ፣ መንደሩም ተበተነ፣ ልማቱም እንደቆመ ቀረ። ይኼኛውስ ምን የተለየ ያደርገዋል?

READ THE REPORT IN PDF

ቸር ወሬ ያሰማን፣
አሜን

Read Full Post »

የሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ በመላው ዓለም ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን በሙሉ!

Read Full Post »



እንደሚታወቀው በመጪው ግንቦት ፳፯ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም. በመላው ዓለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ተዘጋጅቷል፥ ሰልፉም የኢትዮጵያ መንግሥት በሰሜኑ ሀገራችን ክፍል በሚገኘው ታላቁ የዋልድባ ገዳም አካባቢ የወልቃይት ስኳር ፋብሪካ ግንባታ፣ የፓርክ ይዞታ፣ እንዲሁም የመንገድ ጥርጊያ እሰራለሁ በሚል ሰበብ የዋልድባ ገዳም ይዞታን የተለያዩ ከባድና ቀላል የእርሻ መሳሪያዎችን በመጠቀም አጽመ ቅዱሳንን በማፍለስ፣ ቦታውንም በዶዘር በማረስ መጠነ ሰፊ የሆነ የጥፋት ዘማቻ ከጀመረ ውሎ አድሯል፤ ቦታው የመድኃኒዓለም ስም የሚወደስበት የሚሰለስበት ቅዱስ ቦታ ነው ያሉ ገዳማውያኑም አቤቱታቸውን ከማይፀብሪ አውራጃ እስከ ጠቅላይ ሚንስትሩ ጽ/ቤት ብሎም በመንበረ ፖትሪያሪኩ ጽ/ቤት ድረስ አቅርበው ነበር ነገር ግን ሰሚ ሊያገኙ አልቻሉም። ለዚህም ነው ድምጻቸው ድምጻችን ነው፣ አቤቱታቸው አቤቱታችን ነው፣ መገፋታቸው መገፋታችን ነው ያልን በተለያዩ ዓለማት የምንኖር ትውልደ ኢትዮጵያውያን የሆንን በሃገር ውስጥ የገዳማውያኑን አቤቱታ ሊሰማ የፈቀደ ከመንግሥትም ከቤተክህነቱም ስለሌለ እኛ ልጆቻቸው አቤቱታቸውን ለዓለም ሕብረተሰብ ማሰማት ይኖርብናል በሚል ቅን ሀሳብ በመጪው ግንቦት ፳፯ የመድኅኒዓለም እለት በተለያዩ የዓለማችን ክፍል የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለማሳወቅ የምንወጣው፥ 
በኢትዮጵያ ሀገራችን የሚገኙ ኦርቶዶክሳዊያን ከገዳማውያኑ ጋር የዓላማ አንድነታችንን ለማሳየት፣ ይልቁንም እንደሻማ ቀልጠው ብርሃን ለሆኑት ለክርስቶስ ፍቅር ብለው በረሃ ለበረሃ ለተቅበዘበዙት አባቶቻችን መነኩሳት በዚሁ እለት የመድኅኒዓለም እለት የመድኀኒዓለም ታቦት ባለበት ቦታ ሁሉ አባቶች፣ እናቶች፣ እህቶች፣ ወንድሞች በአንድነት በፍቅር ሆነን እነዚህን ሦስት መዝሙራት እየዘመርን የአላማ አንድነታችንን እንድናሳውቅ መልክታችንን በመላው የኢትዮጵያ ለሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን በሙሉ ያስተላልፉን።
በአዲስ አበባ (ቦሌ መድኅኒዓለም)፣ በመቌሌ፣ በጎንደር፣ በባሕር ዳር፣ ደብረ ማርቆስ፣ በደሴ፣ በሸዋ፣ በደብረዘይት፣ በናዝሬት፣ በነቀምት፣ በአርዚ፣ በሐዋሳ፣ በዲላ፣ በይርጋለም፣ በኢሉባቡር፣ በጅማ፣ በሐረር፣ በድሬደዋ፣ በይርጋለም፣ በሻሸመኔ፣ በአባ ምንጭ፣ እና በደብረብርሃን በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ከተሞች በሙሉ በሚገኙ የመድኀኒዓለም ደብር በሙሉ በግንቦት ፳፯ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም. 


፩ኛ/ “ማርያም ሐዘነ ልቦና ታቀላለች”
፪ኛ/ “መድኀኒዓለም አዳነን በማይሻር ቃሉ”
፫ኛ/ “ኀይል የእግዚአብሔር ነው”


ማሳሰቢያ: ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ፍፁም ሰላማዊ ናትና መርኃ ግብሩሰላማይሆን ዘንድ በታላቅ አክብሮት እንጠይቃለን

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ገዳማቶቿን በቸርነቱ ይጠብቅልን !!!

በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ዋልድባን ለመታደግ የሚንቀሳቀሰው ዓለም አቀፍ ጊዚያዊ 

ኮሚቴ
ሰሜን አሜሪካ

Read Full Post »

በJune 4, 2012 ለተጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ከተለያዩ የአሜሪካን ከተሞች ለምትመጡ የሰላማዊ ሰልፉ እድምተኞች በተጠቀሱት የስቴት መሰረት የትራቭል አሬንጅመቶችን ከአሁኑ እንድታደርጉ በቅድሚያ እናስገነዝባለን። የስቴት ተወካዮችም ዝግጅታችሁን በዚሁ መሰረት እንድታደርጉ በቅድሚያ ለማስገንዘብ እንወዳለን።
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያ ሃገራችንን እና ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን በረደኤት ይጠብቅልን አሜን።

Read Full Post »

Older Posts »